አንደኛ ዜና መዋዕል
10 ፍልስጤማውያንም ከእስራኤል ጋር እየተዋጉ ነበር። የእስራኤልም ሰዎች ከፍልስጤማውያን ፊት ሸሹ፤ ብዙዎቹም በጊልቦአ ተራራ ላይ ተገደሉ።+ 2 ፍልስጤማውያን ሳኦልንና ወንዶች ልጆቹን እግር በእግር ተከታተሏቸው፤ ፍልስጤማውያንም የሳኦልን ወንዶች ልጆች ዮናታንን፣ አቢናዳብንና ሜልኪሳን+ መተው ገደሏቸው። 3 ውጊያው በሳኦል ላይ በረታ፤ ቀስተኞቹም አገኙት፤ ደግሞም አቆሰሉት።+ 4 ከዚያም ሳኦል ጋሻ ጃግሬውን “እነዚህ ያልተገረዙ ሰዎች መጥተው በጭካኔ እንዳያሠቃዩኝ*+ ሰይፍህን መዘህ ውጋኝ” አለው። ጋሻ ጃግሬው ግን እጅግ ፈርቶ ስለነበር ፈቃደኛ አልሆነም። በመሆኑም ሳኦል ሰይፉን ወስዶ በላዩ ላይ ወድቆ ሞተ።+ 5 ጋሻ ጃግሬው ሳኦል መሞቱን ሲያይ እሱም በራሱ ሰይፍ ላይ ወድቆ ሞተ። 6 ስለዚህ ሳኦልም ሆነ ሦስት ወንዶች ልጆቹ ሞቱ፤ የቤቱም ሰዎች ሁሉ አብረው ሞቱ።+ 7 በሸለቆው ውስጥ የነበሩት* የእስራኤል ሰዎች ሁሉ ሠራዊቱ መሸሹን እንዲሁም ሳኦልና ልጆቹ መሞታቸውን ባዩ ጊዜ ከተሞቻቸውን ጥለው ሸሹ፤ ከዚያም ፍልስጤማውያን መጥተው ከተሞቹን ያዙ።
8 በማግስቱ ፍልስጤማውያን የሞቱትን ሰዎች ልብስና ትጥቅ ለመግፈፍ ሲመጡ ሳኦልንና ወንዶች ልጆቹን በጊልቦአ ተራራ ላይ ወድቀው አገኟቸው።+ 9 ስለሆነም ሳኦልን ገፈፉት፤ ራሱን ከቆረጡና የጦር ትጥቁን ከወሰዱ በኋላ ወሬው ለጣዖቶቻቸውና+ ለሕዝቡ እንዲዳረስ ወደ ፍልስጤም ምድር ሁሉ መልእክት ላኩ። 10 ከዚያም የጦር ትጥቁን በአምላካቸው ቤት* አስቀመጡት፤ ራሱን ደግሞ በዳጎን ቤት+ ላይ ቸነከሩት።
11 በጊልያድ በምትገኘው በኢያቢስ+ የሚኖሩ ሰዎች በሙሉ ፍልስጤማውያን በሳኦል ላይ ያደረጉትን ሁሉ ሲሰሙ+ 12 ተዋጊዎቹ ሁሉ ተነሱ፤ የሳኦልንና የልጆቹንም አስከሬን ተሸክመው ወደ ኢያቢስ አመጡ። ከዚያም አፅማቸውን በኢያቢስ በሚገኝ ትልቅ ዛፍ ሥር ቀበሩ፤+ ለሰባት ቀንም ጾሙ።
13 ስለዚህ ሳኦል ለይሖዋ ታማኝ ሳይሆን በመቅረቱ ሞተ፤ ምክንያቱም የይሖዋን ቃል አልታዘዘም፤+ ደግሞም መናፍስት ጠሪን አማከረ፤+ 14 ይሖዋንም አልጠየቀም። ስለሆነም ለሞት አሳልፎ ሰጠው፤ ንግሥናውም ለእሴይ ልጅ ለዳዊት እንዲተላለፍ አደረገ።+