ኢሳይያስ
58 “ጉሮሮህ እስኪሰነጠቅ ጩኽ፤ ምንም አትቆጥብ!
ድምፅህን እንደ ቀንደ መለከት አሰማ።
ለሕዝቤ ዓመፃቸውን፣
ለያዕቆብ ቤት ኃጢአታቸውን አውጅ።+
በጽድቅ እንድፈርድላቸው ይጠይቃሉ፤
ወደ አምላክ መቅረብ ደስ ያሰኛቸዋል፦+
3 ‘ስንጾም የማታየው ለምንድን ነው?+
ራሳችንን* ስናጎሳቁል የማታስተውለውስ ለምንድን ነው?’+
4 ጾማችሁ በጭቅጭቅና በጥል ያበቃል፤
እንዲሁም ያለርኅራኄ በቡጢ ትማታላችሁ።
ዛሬ እንደምትጾሙት እየጾማችሁ ድምፃችሁ በሰማይ ሊሰማ አይችልም።
5 እኔ የመረጥኩት ጾም እንዲህ ሊሆን ይገባል?
ሰው ራሱን* የሚያጎሳቁልበት፣
እንደ እንግጫ ራሱን የሚደፋበት፣
መኝታውን በማቅና በአመድ ላይ የሚያነጥፍበት ቀን መሆን አለበት?
እናንተ ጾም የምትሉት፣ ይሖዋንም ደስ የሚያሰኝ ቀን ብላችሁ የምትጠሩት ይህን ነው?
6 አይደለም፤ እኔ የመረጥኩት ጾም ይህ ነው፦
የክፋትን የእግር ብረት እንድታስወግዱ፣
የቀንበርን ማሰሪያ እንድትፈቱ፣+
የተጨቆኑትን በነፃ እንድትለቁ፣+
ቀንበርንም ሁሉ እንድትሰብሩ ነው፤
7 ምግብህን ለተራበው እንድታካፍል፣+
ድሆችንና ቤት የሌላቸውን ወደ ቤትህ እንድታስገባ፣
የተራቆተ ሰው ስታይ እንድታለብስ፣+
ለሥጋ ዘመድህም ጀርባህን እንዳትሰጥ ነው።
8 በዚህ ጊዜ ብርሃንህ እንደ ንጋት ጮራ ይፈነጥቃል፤+
ፈውስህም ፈጥኖ ይመጣል።
ጽድቅህም በፊትህ ይሄዳል፤
የይሖዋም ክብር ደጀን ይሆንልሃል።+
9 የዚያን ጊዜ ትጣራለህ፤ ይሖዋም ይመልስልሃል፤
እርዳታ ለማግኘት ትጮኻለህ፤ እሱም ‘አለሁልህ!’ ይልሃል።
ከመካከልህ ቀንበሩን ብታስወግድ
እንዲሁም ጣትህን መቀሰርና ተንኮል ያዘለ ንግግር መናገር ብትተው፣+
10 ለተራበው ሰው አንተ ራስህ* የምትፈልገውን ነገር ብታደርግለት፣+
የተጎሳቆሉትንም ብታረካ፣*
ያን ጊዜ ብርሃንህ በጨለማ እንኳ ቦግ ብሎ ይበራል፤
ጨለማህም እንደ ቀትር ብርሃን ይሆናል።+
11 ይሖዋ ምንጊዜም ይመራሃል፤
ደረቅ በሆነ ምድርም እንኳ ፍላጎትህን ያረካል፤*+
አጥንቶችህን ያበረታል፤
አንተም ውኃ እንደሚጠግብ የአትክልት ቦታና
ውኃው እንደማይቋረጥ ምንጭ ትሆናለህ።+