ሐሙስ፣ መስከረም 11
ለእነሱ ያላችሁን ፍቅር እውነተኝነት በተጨባጭ አስመሥክሩ።—2 ቆሮ. 8:24
ወንድሞቻችንና እህቶቻችን ጓደኞቻችን እንዲሆኑ በመፍቀድ ፍቅር ማሳየት እንችላለን። (2 ቆሮ. 6:11-13) በብዙዎቹ ጉባኤዎች ውስጥ የተለያየ አስተዳደግና ባሕርይ ያላቸው ወንድሞችና እህቶች ይገኛሉ። ባሏቸው መልካም ባሕርያት ላይ በማተኮር ለሁሉም ወንድሞቻችንና እህቶቻችን ያለንን ፍቅር ማሳደግ እንችላለን። ሌሎችን በይሖዋ ዓይን በማየት እንደምንወዳቸው እናስመሠክራለን። በታላቁ መከራ ወቅት ፍቅር በጣም አስፈላጊ ነገር ይሆናል። መከራው ሲጀምር ጥበቃ ማግኘት የምንችለው የት ነው? ይሖዋ በጥንቷ ባቢሎን ላይ ጥቃት ሲሰነዘር ለሕዝቡ ምን መመሪያ እንደሰጠ እንመልከት፦ “ሕዝቤ ሆይ፣ ሂድ ወደ ውስጠኛው ክፍልህ ግባ፤ በርህንም ከኋላህ ዝጋ። ቁጣው እስኪያልፍ ድረስ ለጥቂት ጊዜ ተሸሸግ።” (ኢሳ. 26:20) እነዚህ ቃላት ታላቁን መከራ ለምንጋፈጥ ክርስቲያኖችም የሚሠሩ ይመስላል። w23.07 6-7 አን. 14-16
ዓርብ፣ መስከረም 12
የዚህ ዓለም ትእይንት እየተለዋወጠ ነው።—1 ቆሮ. 7:31
ምክንያታዊ ነው የሚል ስም አትርፉ። ራሳችሁን እንዲህ እያላችሁ ጠይቁ፦ ‘ሰዎች ምክንያታዊ፣ እሺ ባይና ሰው የሚለኝን የምሰማ እንደሆንኩ ይሰማቸዋል? ወይስ ድርቅ ያልኩ፣ ግትርና አልሰማም ባይ አድርገው ይመለከቱኛል? ሌሎችን ለማዳመጥ፣ የሚቻል ከሆነም ሐሳባቸውን ለመቀበል ፈቃደኛ ነኝ?’ ይበልጥ ምክንያታዊ በሆንን መጠን ይሖዋንና ኢየሱስን ይበልጥ እንመስላለን። ምክንያታዊ መሆን፣ ለውጦች ሲያጋጥሙን ሁኔታዎችን እንደአመጣጣቸው ለማስተናገድ ያስችለናል። አንዳንድ ጊዜ ለውጦች ባልጠበቅነው አቅጣጫ ሕይወታችንን ሊያከብዱብን ይችላሉ። በድንገት ከባድ የጤና ችግር ሊያጋጥመን ይችላል፤ ወይም በምንኖርበት አካባቢ በኢኮኖሚው አሊያም በፖለቲካው ሥርዓት ላይ ድንገተኛ ለውጥ ተከስቶ ኑሯችን ሊመሰቃቀልብን ይችላል። (መክ. 9:11) የአገልግሎት ምድብ ለውጥ እንኳ ፈተና የሚሆንበት ጊዜ አለ። የሚከተሉትን አራት እርምጃዎች ከወሰድን አዲሱን ሁኔታ መልመድ ቀላል ይሆንልናል፦ (1) እውነታውን መቀበል፣ (2) ነገን አሻግሮ ማየት፣ (3) በጎ በጎውን ማሰብ እንዲሁም (4) ሌሎችን መርዳት። w23.07 21-22 አን. 7-8
ቅዳሜ፣ መስከረም 13
አንተ እጅግ የተወደድክ ነህ።—ዳን. 9:23
ነቢዩ ዳንኤል በባቢሎናውያን ተማርኮ ወደ ሩቅ አገር በተወሰደበት ወቅት ገና ወጣት ነበር። ዳንኤል ልጅ ቢሆንም የባቢሎን ባለሥልጣናት በጣም ተደመሙበት። እነሱ ያዩት ‘ውጫዊ ገጽታውን’ ማለትም ‘እንከን የሌለበት፣ መልከ መልካም’ እና ከታዋቂ ቤተሰብ የመጣ መሆኑን ነው። (1 ሳሙ. 16:7) በመሆኑም ባቢሎናውያን በቤተ መንግሥቱ ውስጥ እንዲያገለግል አሠለጠኑት። (ዳን. 1:3, 4, 6) ይሖዋ ዳንኤልን የወደደው ምን ዓይነት ሰው ለመሆን እንደመረጠ ስላየ ነው። እንዲያውም ይሖዋ ዳንኤልን ለበርካታ አሥርተ ዓመታት እሱን በታማኝነት ካገለገሉት ከኖኅና ከኢዮብ ጋር አብሮ የጠቀሰው ዳንኤል ገና በአሥራዎቹ ዕድሜ መጨረሻ ወይም በሃያዎቹ ዕድሜ መጀመሪያ ሳለ ሊሆን ይችላል። (ዘፍ. 5:32፤ 6:9, 10፤ ኢዮብ 42:16, 17፤ ሕዝ. 14:14) ደግሞም ዳንኤል ባሳለፈው ረጅምና አስደናቂ ሕይወት በሙሉ ይሖዋ ይወደው ነበር።—ዳን. 10:11, 19፤ w23.08 2 አን. 1-2