ቅዳሜ፣ መስከረም 13
አንተ እጅግ የተወደድክ ነህ።—ዳን. 9:23
ነቢዩ ዳንኤል በባቢሎናውያን ተማርኮ ወደ ሩቅ አገር በተወሰደበት ወቅት ገና ወጣት ነበር። ዳንኤል ልጅ ቢሆንም የባቢሎን ባለሥልጣናት በጣም ተደመሙበት። እነሱ ያዩት ‘ውጫዊ ገጽታውን’ ማለትም ‘እንከን የሌለበት፣ መልከ መልካም’ እና ከታዋቂ ቤተሰብ የመጣ መሆኑን ነው። (1 ሳሙ. 16:7) በመሆኑም ባቢሎናውያን በቤተ መንግሥቱ ውስጥ እንዲያገለግል አሠለጠኑት። (ዳን. 1:3, 4, 6) ይሖዋ ዳንኤልን የወደደው ምን ዓይነት ሰው ለመሆን እንደመረጠ ስላየ ነው። እንዲያውም ይሖዋ ዳንኤልን ለበርካታ አሥርተ ዓመታት እሱን በታማኝነት ካገለገሉት ከኖኅና ከኢዮብ ጋር አብሮ የጠቀሰው ዳንኤል ገና በአሥራዎቹ ዕድሜ መጨረሻ ወይም በሃያዎቹ ዕድሜ መጀመሪያ ሳለ ሊሆን ይችላል። (ዘፍ. 5:32፤ 6:9, 10፤ ኢዮብ 42:16, 17፤ ሕዝ. 14:14) ደግሞም ዳንኤል ባሳለፈው ረጅምና አስደናቂ ሕይወት በሙሉ ይሖዋ ይወደው ነበር።—ዳን. 10:11, 19፤ w23.08 2 አን. 1-2
እሁድ፣ መስከረም 14
ስፋቱ፣ ርዝመቱ፣ ከፍታውና ጥልቀቱ ምን ያህል እንደሆነ [በሚገባ ተረዱ]።—ኤፌ. 3:18
አንድን ቤት ለመግዛት ስታስብ የምትገዛውን ቤት ከሁሉም አቅጣጫ በአካል በደንብ ማየት እንደምትፈልግ ምንም ጥያቄ የለውም። መጽሐፍ ቅዱስን ስናነብና ስናጠናም ተመሳሳይ ነገር ማድረግ እንችላለን። በጥድፊያ ካነበብከው፣ የምትማረው “የአምላክን ቅዱስ መልእክት መሠረታዊ ነገሮች” ብቻ ነው። (ዕብ. 5:12) ከዚህ ይልቅ ልክ እንደ ቤቱ ሁሉ ወደ ውስጥ ገብተህ ዝርዝር መረጃዎችን ለመመርመር ጥረት አድርግ። መጽሐፍ ቅዱስን ማጥናት የምትችልበት አንዱ ግሩም መንገድ በውስጡ ያሉት መልእክቶች እንዴት እንደሚያያዙ ማስተዋል ነው። የምታምንባቸውን እውነቶች ምንነት ብቻ ሳይሆን በእነዚህ እውነቶች የምታምነው ለምን እንደሆነም ለመመርመር ጥረት አድርግ። የአምላክን ቃል በሚገባ ለመረዳት ጥልቀት ያላቸውን የመጽሐፍ ቅዱስ እውነቶች መማር ይኖርብናል። ሐዋርያው ጳውሎስ ክርስቲያን ወንድሞቹና እህቶቹ የእውነት ‘ስፋት፣ ርዝመት፣ ከፍታና ጥልቀት ምን ያህል እንደሆነ በሚገባ መረዳት እንዲችሉ’ የአምላክን ቃል በትጋት እንዲያጠኑ አበረታቷቸዋል። እንዲህ ካደረጉ በእምነታቸው ይበልጥ ‘ሥር መስደድና መታነጽ’ ይችላሉ። (ኤፌ. 3:14-19) እኛም ይህንኑ ልናደርግ ይገባል። w23.10 18 አን. 1-3
ሰኞ፣ መስከረም 15
ወንድሞች፣ በይሖዋ ስም የተናገሩትን ነቢያት መከራ በመቀበልና ትዕግሥት በማሳየት ረገድ አርዓያ አድርጋችሁ ተመልከቷቸው።—ያዕ. 5:10
መጽሐፍ ቅዱስ ትዕግሥት ያሳዩ በርካታ ሰዎችን ምሳሌ ይዟል። በግል ጥናትህ ላይ የእነዚህን ሰዎች ምሳሌ ለመመርመር ለምን አትሞክርም? ለአብነት ያህል፣ ዳዊት የእስራኤል ንጉሥ እንዲሆን የተቀባው ገና በልጅነቱ ቢሆንም ንግሥናውን እስኪቀበል ድረስ ለበርካታ ዓመታት መጠበቅ አስፈልጎታል። ስምዖን እና ሐና፣ ተስፋ የተሰጠበት መሲሕ እስኪመጣ በሚጠባበቁበት ወቅት ይሖዋን በታማኝነት ያገለግሉ ነበር። (ሉቃስ 2:25, 36-38) እንዲህ ያሉትን ዘገባዎች በምታጠናበት ወቅት የእነዚህን ጥያቄዎች መልስ ለመፈለግ ጥረት አድርግ፦ ይህ ሰው ትዕግሥት እንዲያሳይ የረዳው ምን ሊሆን ይችላል? ትዕግሥተኛ መሆኑ የጠቀመው እንዴት ነው? የእሱን ምሳሌ መከተል የምችለው እንዴት ነው? ትዕግሥት ስላላሳዩ ሰዎች ማጥናትህም ሊጠቅምህ ይችላል። (1 ሳሙ. 13:8-14) የሚከተሉትን ጥያቄዎች ልታነሳ ትችላለህ፦ ‘ትዕግሥት እንዳያሳይ ያደረገው ምን ሊሆን ይችላል? ትዕግሥት አለማሳየቱ ምን መዘዝ አስከትሎበታል?’ w23.08 25 አን. 15