እሁድ፣ መስከረም 14
ስፋቱ፣ ርዝመቱ፣ ከፍታውና ጥልቀቱ ምን ያህል እንደሆነ [በሚገባ ተረዱ]።—ኤፌ. 3:18
አንድን ቤት ለመግዛት ስታስብ የምትገዛውን ቤት ከሁሉም አቅጣጫ በአካል በደንብ ማየት እንደምትፈልግ ምንም ጥያቄ የለውም። መጽሐፍ ቅዱስን ስናነብና ስናጠናም ተመሳሳይ ነገር ማድረግ እንችላለን። በጥድፊያ ካነበብከው፣ የምትማረው “የአምላክን ቅዱስ መልእክት መሠረታዊ ነገሮች” ብቻ ነው። (ዕብ. 5:12) ከዚህ ይልቅ ልክ እንደ ቤቱ ሁሉ ወደ ውስጥ ገብተህ ዝርዝር መረጃዎችን ለመመርመር ጥረት አድርግ። መጽሐፍ ቅዱስን ማጥናት የምትችልበት አንዱ ግሩም መንገድ በውስጡ ያሉት መልእክቶች እንዴት እንደሚያያዙ ማስተዋል ነው። የምታምንባቸውን እውነቶች ምንነት ብቻ ሳይሆን በእነዚህ እውነቶች የምታምነው ለምን እንደሆነም ለመመርመር ጥረት አድርግ። የአምላክን ቃል በሚገባ ለመረዳት ጥልቀት ያላቸውን የመጽሐፍ ቅዱስ እውነቶች መማር ይኖርብናል። ሐዋርያው ጳውሎስ ክርስቲያን ወንድሞቹና እህቶቹ የእውነት ‘ስፋት፣ ርዝመት፣ ከፍታና ጥልቀት ምን ያህል እንደሆነ በሚገባ መረዳት እንዲችሉ’ የአምላክን ቃል በትጋት እንዲያጠኑ አበረታቷቸዋል። እንዲህ ካደረጉ በእምነታቸው ይበልጥ ‘ሥር መስደድና መታነጽ’ ይችላሉ። (ኤፌ. 3:14-19) እኛም ይህንኑ ልናደርግ ይገባል። w23.10 18 አን. 1-3
ሰኞ፣ መስከረም 15
ወንድሞች፣ በይሖዋ ስም የተናገሩትን ነቢያት መከራ በመቀበልና ትዕግሥት በማሳየት ረገድ አርዓያ አድርጋችሁ ተመልከቷቸው።—ያዕ. 5:10
መጽሐፍ ቅዱስ ትዕግሥት ያሳዩ በርካታ ሰዎችን ምሳሌ ይዟል። በግል ጥናትህ ላይ የእነዚህን ሰዎች ምሳሌ ለመመርመር ለምን አትሞክርም? ለአብነት ያህል፣ ዳዊት የእስራኤል ንጉሥ እንዲሆን የተቀባው ገና በልጅነቱ ቢሆንም ንግሥናውን እስኪቀበል ድረስ ለበርካታ ዓመታት መጠበቅ አስፈልጎታል። ስምዖን እና ሐና፣ ተስፋ የተሰጠበት መሲሕ እስኪመጣ በሚጠባበቁበት ወቅት ይሖዋን በታማኝነት ያገለግሉ ነበር። (ሉቃስ 2:25, 36-38) እንዲህ ያሉትን ዘገባዎች በምታጠናበት ወቅት የእነዚህን ጥያቄዎች መልስ ለመፈለግ ጥረት አድርግ፦ ይህ ሰው ትዕግሥት እንዲያሳይ የረዳው ምን ሊሆን ይችላል? ትዕግሥተኛ መሆኑ የጠቀመው እንዴት ነው? የእሱን ምሳሌ መከተል የምችለው እንዴት ነው? ትዕግሥት ስላላሳዩ ሰዎች ማጥናትህም ሊጠቅምህ ይችላል። (1 ሳሙ. 13:8-14) የሚከተሉትን ጥያቄዎች ልታነሳ ትችላለህ፦ ‘ትዕግሥት እንዳያሳይ ያደረገው ምን ሊሆን ይችላል? ትዕግሥት አለማሳየቱ ምን መዘዝ አስከትሎበታል?’ w23.08 25 አን. 15
ማክሰኞ፣ መስከረም 16
አንተ የአምላክ ቅዱስ አገልጋይ እንደሆንክ አምነናል፤ ደግሞም አውቀናል።—ዮሐ. 6:69
ሐዋርያው ጴጥሮስ ታማኝ ነበር፤ ምንም ነገር ኢየሱስን መከተሉን እንዲያስቆመው አልፈቀደም። በአንድ ወቅት ኢየሱስ የተናገረውን ነገር ደቀ መዛሙርቱ መረዳት ባቃታቸው ጊዜ ጴጥሮስ ታማኝ መሆኑን አሳይቷል። (ዮሐ. 6:68) ብዙዎች፣ ኢየሱስ ማብራሪያ እንዲሰጣቸው ሳይጠብቁ እሱን መከተላቸውን አቆሙ። ጴጥሮስ ግን እንደዚያ አላደረገም። “የዘላለም ሕይወት ቃል” ያለው ኢየሱስ ብቻ እንደሆነ ተገንዝቦ ነበር። ኢየሱስ ጴጥሮስና ሌሎቹ ሐዋርያት ትተውት እንደሚሄዱ አውቆ ነበር። ያም ቢሆን ኢየሱስ፣ ጴጥሮስ እንደሚመለስና ታማኝ ሆኖ እንደሚቀጥል እርግጠኛ ነበር። (ሉቃስ 22:31, 32) ኢየሱስ “መንፈስ ዝግጁ . . . ሥጋ ግን ደካማ” እንደሆነ ያውቅ ነበር። (ማር. 14:38) በመሆኑም ጴጥሮስ ከካደው በኋላም እንኳ ኢየሱስ ተስፋ አልቆረጠበትም። ኢየሱስ ከሞት ከተነሳ በኋላ ለጴጥሮስ ተገለጠለት፤ በዚህ ወቅት ጴጥሮስ ብቻውን ሳይሆን አይቀርም። (ማር. 16:7፤ ሉቃስ 24:34፤ 1 ቆሮ. 15:5) ቅስሙ የተሰበረው ይህ ሐዋርያ በዚህ ምንኛ ተጽናንቶ ይሆን! w23.09 22 አን. 9-10