ዓርብ፣ መስከረም 19
እርስ በርስ መዋደዳችንን እንቀጥል።—1 ዮሐ. 4:7
ሁላችንም ‘እርስ በርስ መዋደዳችንን መቀጠል’ እንፈልጋለን። ሆኖም ኢየሱስ “የብዙዎች ፍቅር ይቀዘቅዛል” የሚል ማስጠንቀቂያ እንደሰጠ ማስታወስ ይኖርብናል። (ማቴ. 24:12) ኢየሱስ ይህን ሲል የአብዛኞቹ ደቀ መዛሙርቱ ፍቅር እንደሚቀዘቅዝ መናገሩ አልነበረም። ያም ቢሆን፣ በምንኖርበት ዓለም ውስጥ ፍቅር መጥፋቱ ተጽዕኖ እንዳያሳድርብን ልንጠነቀቅ ይገባል። ይህን ሐሳብ በአእምሯችን በመያዝ የሚከተለውን ጥያቄ ለመመለስ እንሞክር፦ ለወንድሞቻችን ያለን ፍቅር ጠንካራ መሆኑን መፈተን የምንችልበት መንገድ አለ? ፍቅራችን ምን ያህል ጠንካራ እንደሆነ መፈተን የምንችልበት አንዱ መንገድ በሕይወታችን ውስጥ የሚያጋጥሙንን አንዳንድ ሁኔታዎች እንዴት እንደምንይዝ መገምገም ነው። (2 ቆሮ. 8:8) ሐዋርያው ጴጥሮስ ከእነዚህ ሁኔታዎች መካከል አንዱን ሲጠቅስ እንዲህ ብሏል፦ “ከሁሉም በላይ አንዳችሁ ለሌላው የጠለቀ ፍቅር ይኑራችሁ፤ ምክንያቱም ፍቅር የኃጢአትን ብዛት ይሸፍናል።” (1 ጴጥ. 4:8) በመሆኑም የሌሎች ድክመትና አለፍጽምና ፍቅራችንን ሊፈትነው ይችላል። w23.11 10-11 አን. 12-13
ቅዳሜ፣ መስከረም 20
እርስ በርሳችሁ [ተዋደዱ]።—ዮሐ. 13:34
በጉባኤው ውስጥ ላሉ አንዳንድ ክርስቲያኖች ፍቅር እያሳየን ለሌሎቹ ግን የማናሳይ ከሆነ ኢየሱስ ስለ ፍቅር የሰጠውን ትእዛዝ ተከትለናል ሊባል አይችልም። እርግጥ ነው፣ እኛም እንደ ኢየሱስ ከአንዳንዶቹ ወንድሞቻችን ጋር ይበልጥ እንቀራረብ ይሆናል። (ዮሐ. 13:23፤ 20:2) ሆኖም ሐዋርያው ጴጥሮስ ለሁሉም ወንድሞቻችንና እህቶቻችን “የወንድማማች መዋደድ” ማለትም በቤተሰብ ውስጥ ያለው ዓይነት ፍቅር ሊኖረን እንደሚገባ አሳስቦናል። (1 ጴጥ. 2:17) ጴጥሮስ “እርስ በርሳችሁ አጥብቃችሁ ከልብ ተዋደዱ” የሚል ማበረታቻ ሰጥቶናል። (1 ጴጥ. 1:22) ‘አጥብቆ መዋደድ’ የሚለው አገላለጽ ፍቅር ማሳየት በሚከብደን ጊዜም ጭምር መዋደድን ያካትታል። ለምሳሌ አንድ ወንድም ቅር ቢያሰኘን ወይም በሆነ መንገድ ቢጎዳንስ? የሚቀናን ፍቅር ማሳየት ሳይሆን አጸፋውን መመለስ ሊሆን ይችላል። ነገር ግን ጴጥሮስ አጸፋ መመለስ አምላክን እንደማያስደስተው ከኢየሱስ ተምሯል። (ዮሐ. 18:10, 11) ጴጥሮስ “ክፉን በክፉ ወይም ስድብን በስድብ አትመልሱ። ከዚህ ይልቅ ባርኩ” ሲል ጽፏል። (1 ጴጥ. 3:9) ሌሎችን አጥብቀን የምንወድ ከሆነ ደግነትና አሳቢነት ለማሳየት እንነሳሳለን። w23.09 28-29 አን. 9-11
እሁድ፣ መስከረም 21
ሴቶችም እንደዚሁ . . . በልማዶቻቸው ልከኞችና በሁሉም ነገር ታማኞች ሊሆኑ ይገባል።—1 ጢሞ. 3:11
አንድ ልጅ አድጎ ትልቅ ሰው የሚሆንበት ፍጥነት በጣም ያስገርመናል። ይህ እድገት በራሱ የሚከናወን ይመስል ይሆናል። ይሁንና እድገት አድርጎ ክርስቲያናዊ ጉልምስና ላይ መድረስ በራሱ የሚመጣ ነገር አይደለም። (1 ቆሮ. 13:11፤ ዕብ. 6:1) እዚህ ግብ ላይ ለመድረስ ከይሖዋ ጋር የጠበቀ ወዳጅነት ሊኖረን ይገባል። በተጨማሪም አምላካዊ ባሕርያትን ለማዳበር፣ ጠቃሚ ክህሎቶችን ለመማር እንዲሁም ወደፊት ለምንቀበላቸው ኃላፊነቶች ለመዘጋጀት የአምላክ ቅዱስ መንፈስ ያስፈልገናል። (ምሳሌ 1:5) ይሖዋ ሰዎችን የፈጠራቸው ወንድ እና ሴት አድርጎ ነው። (ዘፍ. 1:27) ወንዶችና ሴቶች አካላዊ ልዩነት እንዳላቸው ግልጽ ነው፤ ይሁንና በሌሎች መንገዶችም ይለያያሉ። ለምሳሌ ይሖዋ ወንዶችንና ሴቶችን የፈጠራቸው የየራሳቸው ሚና ሰጥቶ ነው። በመሆኑም የተሰጣቸውን ኃላፊነት ለመወጣት የሚያስችሉ ባሕርያትና ክህሎቶች ያስፈልጓቸዋል።—ዘፍ. 2:18፤ w23.12 18 አን. 1-2