የብቸኝነት ኑሮ ያሳለፈው ሰው
“የአንዲት ድሀ ሴት ልጅ ነው፤ የተወለደው በአንዲት የማትታወቅ መንደር ውስጥ ነበር። ያደገውም በሌላ አነስተኛ መንደር ውስጥ ነው፤ ሠላሳ ዓመት እስኪሞላው ድረስ በዚች አነስተኛ መንደር ውስጥ በሚገኝ የአናጢ ቤት ውስጥ ሠርቷል። ከዚያ በኋላ ለሦስት ዓመታት ያህል ከቦታ ወደ ቦታ እየተዘዋወረ ሰብኳል።
“መጽሐፍ ጽፎ አያውቅም። ሥልጣን አልነበረውም። ቤተሰብም ሆነ የራሱ ቤት ኖሮት አያውቅም። ኮሌጅ አልገባም። ወደ ትልቅ ከተማ ሄዶ አያውቅም። ከተወለደበት ቦታ አንሥቶ ከሦስት መቶ ኪሎ ሜትር በላይ ተጉዞ አያውቅም። አንድን ሰው ታላቅ ከሚያሰኙት ነገሮች አንዱንም አላደረገም። ከራሱ በቀር ለብቃቱ መረጃ የሚሆን አንዳችም ነገር አልነበረውም።
“የሕዝብ ተቃውሞ ሲዥጎደጎድበት ገና ሠላሳ ሦስት ዓመቱ ነበር። ወዳጆቹ ጥለውት ሸሹ። በጠላቶቹ እጅ አልፎ ተሰጠ፤ የሕዝብ መሳቂያና መሳለቂያ በመሆን ተንገላታ። በሁለት ሌቦች መካከል [በእንጨት] ላይ ተቸነከረ። እርሱ ሊሞት በሚያጣጥርበት ጊዜ የሰቀሉት ሰዎች በምድር ላይ ባፈራት ብቸኛ ንብረቱ በሆነችው በልብሱ ላይ ዕጣ ይጣጣሉ ነበር። ከሞተ በኋላም አዘኔታ ባሳየው ወዳጁ አማካኝነት በውሰት በተገኘች መቃብር ውስጥ ተቀበረ።
“ይህ ከሆነ አሥራ ዘጠኝ መቶ ዘመናት ካለፉ በኋላ ይህ ሰው የመላውን የሰው ዘር ትኩረት የሳበ ታላቅ ሰውና የሰው ልጆች እድገት መሪ በመሆን እስከ ጊዜያችን ድረስ ሊዘልቅ ችሏል። እስከዛሬ ድረስ በጦርነት አውድማ የተሰለፉ ሠራዊቶች በሙሉ፣ በባህር ላይ የዘመቱ የባህር ኃይል ወታደሮች በሙሉ፣ የፓርላማ ወንበሮችን የተቆናጠጡ ሰዎች በሙሉ፣ ሲገዙ የኖሩ ነገሥታት በሙሉ በአንድ ላይ ቢጠቃለሉ የብቸኝነት ኑሮ ያሳለፈውን የዚህን ሰው ያህል በዚህች ፕላኔት ላይ በሚገኘው የሰው ዘር ሕይወት ላይ ከፍተኛ ለውጥ አላመጡም።”a—በኢየሱስ ክርስቶስ ሕይወት ላይ ሐሳብ የሰጠ ስሙ ያልተጠቀሰ ሰው
[የግርጌ ማስታወሻ]
a የብቸኝነት ኑሮ ያሳለፈው ይህ ሰው ዝርዝር ታሪኩ ኒው ዮርክ በሚገኘው የመጠበቂያ ግንብ የመጽሐፍ ቅዱስና ትራክት ማኅበር ታትሞ በወጣው እስከ ዛሬ በምድር ላይ ከኖሩት ሰዎች ሁሉ የሚበልጠው ታላቅ ሰው በተባለው የእንግሊዝኛ መጽሐፍ ላይ ሰፍሮ ይገኛል።