ሕይወት ለአንተ ምን ያህል ውድ ነው?
አንድ በአሥራዎቹ ዕድሜ የሚገኝ ልጅ ከአንድ አፓርታማ ሕንፃ ስምንተኛ ፎቅ ላይ ራሱን በመወርወር ገደለ። ከፍ ካለ ቦታ ላይ ራስን በመወርወር መግደል “ከሥቃይ፣ ከመረበሽ ወይም ከፍርሃት ስሜት ነፃ ያደርጋል፤ ከዚህ ይልቅ ጥሩ ስሜት ያሳድራል” የሚል አንድ መጽሐፍ አንብቦ ነበር። በጃፓን የታተመው የዚህ መጽሐፍ ደራሲ “ራስን መግደልን ከሕይወት አማራጮች አንዱ” እንደሆነ አድርጎ ከማቅረብ ሌላ ያደረገው ነገር እንደሌለ ተናግሯል።
በአሁኑ ወቅት ለሕይወት አክብሮት እንደሌላቸው የሚያሳዩት ራሳቸውን የሚገድሉ ሰዎች ብቻ አይደሉም። ግድ የለሽ የአውቶሞቢል አሽከርካሪዎችም ለሕይወት የሚያሳዩት አክብሮት ይህን ያህል ነው። እንዲያውም አንዳንዶች ጠጥተው ስለሚነዱ ራሳቸውን ይበልጥ ለሞት ያጋልጣሉ።
ሌሎች ደግሞ ለተድላ በሚሰጡት ከፍተኛ ቦታ ለሕይወት ያላቸው ግምት ምን ያህል አናሳ እንደሆነ ያሳያሉ። ሲጋራ አጫሾች ማጨስ ሊገድል የሚችልና ከጊዜ በኋላ ሕይወትን ለሕልፈት መዳረጉ አይቀሬ ነው ቢባልም ሲጋራ ለመተው ፈቃደኛ አይደሉም። ብዙዎች በዚህ በጾታ ስሜት ባበደ ዓለም ውስጥ ንጽሕናቸውን ከመጠበቅ ይልቅ ብዙውን ጊዜ ለሞት የሚዳርገውን የጾታ ብልግና ይፈጽማሉ።
አንዳንዶች የሚያስከትልባቸውን ጠንቅ ካለማወቅም ጭምር ከመጠን በላይ በመብላት፣ ከመጠን በላይ በመጠጣት፣ በቂ የሰውነት እንቅስቃሴ ባለማድረግና ተድላ በማሳደድ ሕይወታቸውን በአጭር ይቀጩታል። ሺኒዮ ኒሽማሩ የተባሉ የጃፓን ደራሲ “ከመጠን በላይ የመብላት ልማድ የአካል አሠራርን ሲያቃውስ፣ ተድላንና ምቾትን ብቻ ማሳደድ ደግሞ የሰዎችን ዕድሜ ያሳጥራል” ሲሉ አስጠንቅቀዋል። አንዳንዶች “ነገ እንሞታለንና እንብላና እንጠጣ” እንዳሉት የጥንት ሰዎች ዓይነት አመለካከት አላቸው።—ኢሳይያስ 22:13፤ 1 ቆሮንቶስ 15:32
አዎን፣ በአሁኑ ወቅት ለሕይወት አክብሮት አለማሳየት ተስፋፍቷል። ስለዚህ ሕይወት ለአንተ ምን ያህል ውድ ነው? የሚለው ጥያቄ መነሣቱ ተገቢ ነው። የተከፈለው ተከፍሎ ሕይወትን ማዳን ይገባልን? አሁን ካለን ሕይወት ይበልጥ ዋጋ ያለው ነገርስ ይኖራልን?