ችግር ለደረሰባቸው ፍቅር ማሳየት
ክርስቲያኖች ችግር ለደረሰባቸው ወንድሞቻቸውና እህቶቻቸው ፍቅር የማሳየት ግዴታም ሆነ መብት አላቸው። (1 ዮሐንስ 3:17, 18) ሐዋርያው ጳውሎስ “ለሰው ሁሉ ይልቁንም ለሃይማኖት ቤተ ሰዎች መልካም እናድርግ” በማለት ጽፏል። (ገላትያ 6:10) ለአራት አሥርተ ዓመታት ገደማ ይሖዋን ሲያገለግል የኖረ አንድ ወንድም በቅርቡ ሚስቱ ታማ በነበረችበት ጊዜና በኋላም በሞተችበት ወቅት የክርስቲያን ወንድማማችነት ፍቅርን ቀምሷል። የሚከተለውን ጽፏል:-
“ሚስቴ ታማ በነበረበት ጊዜ ቤት ሆኜ እሷን አስታምም ስለነበር ለሁለት ወር ያህል ሥራ አቋርጬ ነበር። በጉባኤ ያሉ ጓደኞቻችን በፈቃደኝነት ያደረጉልን እርዳታ ትልቅ ሸክም አቅልሎልናል! ለባንክ ብድር፣ ለመብራትና ለውኃ እንዲሁም ሌሎች ወጪዎችን ለመሸፈን የተከፈለ በርካታ ገንዘብ፣ ‘ተጨማሪ ወጪዎችን ለመሸፈን’ የሚል ጽሕፈት ከሰፈረባቸው ካርዶች ጋር በስጦታ አበርክተውልናል።
“ባለቤቴ ከመሞቷ ከሁለት ሳምንት በፊት የወረዳ የበላይ ተመልካቹ የሚያበረታታ ጉብኝት አደረገልን። ጉባኤው በሳምንቱ መጨረሻ የሚያየውን ስላይድ እንኳን ሳይቀር አሳየን። በወረዳ የበላይ ተመልካቹ የተመራውን የመስክ አገልግሎት ስብሰባ ጨምሮ ስብሰባዎቹን በሙሉ በስልክ መስመር ማዳመጥ ችለን ነበር። በአንደኛው ስብሰባ ወቅት የወረዳ የበላይ ተመልካቹ ለመስክ አገልግሎት ስምሪት ተገኝተው የነበሩት ሁሉ በኅብረት ባለቤቴን ‘እንደምን አለሽ?’ እንዲሉ አድርጓል። ይህም በመሆኑ ምንም እንኳን ባካል ብትርቅም በፍጹም ብቸኝነት ተሰምቷት አያውቅም።
“በሞተች በአንድ ሰዓት ጊዜ ውስጥ የጉባኤያችን ሽማግሌዎች ባጠቃላይ ማለት ይቻላል ወደ ቤቴ መጥተው ነበር። በዛ ዕለት ብቻ ከመቶ በላይ የሚሆኑ ወንድሞችና እህቶች ጠይቀውኛል። ለዚያ ሁሉ ሰው የሚበቃ ምግብ መቅረቡ እንደ ‘ተአምር’ የሚቆጠር ነበር። ስጦታዎቹን፣ የሐዘን መግለጫዎቹን፣ የወንድሞችን የማጽናኛ ቃላትና ለእኔ ሲባል የቀረቡትን ጸሎቶች በሙሉ ዘርዝሬ መጨረስ አልችልም። እነዚህ ሁሉ እጅግ አበረታተውኛል! ወንድሞችን ይበቃል ብዬ እስካስቆምኳቸው ጊዜ ድረስ ምግብ ያመጡልኝ የነበረ ከመሆኑም በላይ ቤቱን በማጽዳት ይረዱኝ ነበር!
“እንደዚህ የመሰለ ልግስና የታከለበት የርኅራኄ፣ የአሳቢነትና የፍቅር መግለጫ ከይሖዋ ድርጅት በስተቀር ሌላ የት ማግኘት እንችላለን? በዛሬው ጊዜ ብዙ ሰዎች ያሏቸው እውነተኛ ጓደኞች በጣት ሊቆጠሩ የሚችሉ ናቸው። እኛ ግን ብዙ መንፈሳዊ ወንድሞችና እህቶች ያቀፈ ትልቅ ቤተሰብ በማግኘታችን ይሖዋ ባርኮናል!”—ማርቆስ 10:29, 30