በድንግልናዋ አገባች?
ብዙ ሠዓሊያንና የቅርጻ ቅርጽ አርቲስቶች ማርያም ዮሴፍን ብታገባም ድንግል ሆና ኖራለች የሚለው አመለካከት ተአማኒነት እንዲኖረው ለማድረግ ሲሉ ዮሴፍን አረጋዊ አድርገው አስቀምጠውታል። እንዲያውም ዮሴፍ ባልዋ ሳይሆን ጠባቂዋ ነው የሚመስለው የሚል ምክንያት ያቀርባሉ። ሆኖም ሊቀ ጳጳስ ጆን ፖል ዳግማዊ በቅርቡ ይህን ጉዳይ በተመለከተ ያላቸውን ከዚህ የተለየ ሐሳብ ተናግረዋል። ዮሴፍ “በወቅቱ አረጋዊ ሰው አልነበረም” በማለት ሐሳብ አቅርበዋል። ከዚህ ይልቅ ዮሴፍ “ከማርያም ጋር በነበረው የትዳር ትስስር በአምላክ ፀጋ ያፈራው ውስጣዊ ፍጽምና ክብረ ንጽሕናዋን ሳይደፍር እንዲኖር አስችሎታል።”
ማርያም ለዘለቄታው ድንግል ሆና እንድትቀጥል ከታቀደ ለምን ታጨች? ሊቀ ጳጳሱ “መጀመሪያውኑ ማርያምና ዮሴፍ ሲተጫጩ ማርያም ድንግል ሆና እንድትኖር ስለነበረው እቅድ አውቀውና ተስማምተው ሊሆን ይችላል” ሲሉ መልሰዋል።
የሆነ ሆኖ መጽሐፍ ቅዱስ ጉዳዩን ከዚህ በተለየ ሁኔታ ይገልጸዋል። የማቴዎስ ዘገባ ዮሴፍ “የበኵር ልጅዋንም እስክትወልድ ድረስ አላወቃትም” በማለት ይገልጻል። (ማቴዎስ 1:25፤ ጋደል አድርገን የጻፍነው እኛ ነን።) ኢየሱስ ከተወለደ በኋላ የዮሴፍና የማርያም የጋብቻ ቁርኝት በጭራሽ በድንግልና አልቀጠለም። ቆየት ብሎ በወንጌል ዘገባ ውስጥ ኢየሱስ ወንድሞችና እህቶች እንዳሉት መገለጹ ለዚህ አንድ ማስረጃ ነው።—ማቴዎስ 13:55, 56
በመሆኑም ኢየሱስን በወለደችበት ጊዜ ማርያም ድንግል እንደነበረች ቢገልጽም ከዮሴፍ ጋር ባሳለፈችው በተቀረው ሕይወቷ ድንግል ሆና ኖራለች ብሎ ለመናገር የሚያበቃ ምንም መሠረት የለም።