ተወቃሹ ማን ነው?
ብዙ ሰዎች ችግሮች ሲገጥሟቸው አምላክን ተወቃሽ ያደርጋሉ። አንድ የመጽሐፍ ቅዱስ ምሳሌ “አንዳንድ ሰዎች በቸልተኛነታቸው፣ በራሳቸው ላይ ጥፋት ያመጣሉ፤ ከዚህ በኋላ እግዚአብሔርን ያማርራሉ” ይላል። (ምሳሌ 19:3 የ1980 ትርጉም) ሆኖም በሰዎች ላይ ለሚደርሱት መከራዎች አምላክን ተጠያቂ ማድረጉ በስካር መንፈስ መኪና በመንዳት ለሚከሰቱት በርካታ አደጋዎች የመኪና አምራቹን ከመውቀስ ተለይቶ አይታይም።
አምላክ በቃሉ በመጽሐፍ ቅዱስ አማካኝነት ለሰው ልጆች የሚጠቅም መመሪያ ሰጥቷል። ብዙ መጻሕፍትን አንድ ላይ አካቶ የያዘውን ይህን መለኮታዊ መጽሐፍ በማጥናትና በውስጡ ባሉት ሕጎችና መሠረታዊ ሥርዓቶች በመመራት በሕይወታችን ላይ ሊደርሱ የሚችሉ ብዙ ጎጂ ሁኔታዎችን ማስቀረት እንችላለን። በአንጻሩ ደግሞ ከአምላክ መመሪያ ውጪ መመላለስ አደጋ ያስከትላል። ለምሳሌ ያህል ከልክ በላይ የሚበሉ፣ የሚያጨሱ፣ የሚሰክሩ ወይም የጾታ ብልግና የሚፈጽሙ ሰዎች ብዙውን ጊዜ አስከፊ የሆነ የጤና ቀውስ ይደርስባቸዋል። (ሉቃስ 21:34፤ 1 ቆሮንቶስ 6:18፤ 2 ቆሮንቶስ 7:1) ክርስቲያኑ ሐዋርያ ጳውሎስ እንዲህ ሲል ጽፏል:- “ሰው የሚዘራውን ሁሉ ያንኑ ደግሞ ያጭዳልና፤ በገዛ ሥጋው የሚዘራ ከሥጋ መበስበስን ያጭዳልና፣ በመንፈስ ግን የሚዘራው ከመንፈስ የዘላለምን ሕይወት ያጭዳል።”—ገላትያ 6:7, 8
ከአምላክ ሕጎችና መሠረታዊ ሥርዓቶች ጋር ተስማምቶ መኖር ምንኛ የተሻለ ነው! እንዲህ ካደረግን አምላክ በነቢዩ ኢሳይያስ በኩል የተናገረው የሚከተለው ቃል በእውን ሲፈጸም ማየት እንችላለን:- “እኔ የሚረባህን ነገር የማስተምርህ በምትሄድባትም መንገድ የምመራህ አምላክህ እግዚአብሔር ነኝ። ትእዛዜን ብትሰማ ኖሮ፣ ሰላምህ እንደ ወንዝ ጽድቅህም እንደ ባሕር ሞገድ በሆነ ነበር።”—ኢሳይያስ 48:17, 18