ሁሉም ቄሶች የሚያስተምሩትን ያምኑበታል?
ሴትዮዋ ባልዋ የሞተው በቅርቡ ነው። የነፍስ አባቷ፣ ባሏ በጣም ጥሩ ሰው ስላልነበረ በቀጥታ ወደ ሰማይ አለመሄዱን፣ በጣም መጥፎም ስላልነበረ በቀጥታ ወደ እሳታማ ሲኦል አለመውረዱን ይገልጹላታል። ከዚህ ይልቅ እንደ ቄሱ አባባል ወደ ሰማይ ለመሄድ ብቁ እስኪሆን ድረስ እየተቀጣ ነው። ሴትዮዋ የነፍስ አባቷ እንዲጸልዩለትና ባሏ ቶሎ ከመንጽሔ እንዲወጣ ገንዘብ ትከፍላቸዋለች። ባሏ የሞተባት ይህች ሴት እሷ በቅንነት የምታምንባቸውን ነገሮች የነፍስ አባቷም ያምኑባቸዋል የሚል ስሜት ስላላት ባደረገችው ነገር ረክታለች።
ይህች ሴት የነፍስ አባቷ በእርግጥ ከሞት በኋላ ቅጣት አለ ብለው እንደማያምኑ ብታውቅ ግራ የምትጋባ ይመስልሃል? ብዙ ሰዎች በርካታ ቁጥር ያላቸው ቀሳውስት ራሳቸው የሚያስተምሩትን አብዛኛውን ነገር እንደማያምኑበት ሲያውቁ በጣም ግራ ይጋባሉ። ናሽናል ካተሊክ ሪፖርተር የተባለው ጋዜጣ “ከጾታ ብልግና የከፋው ሌላ የቀሳውስቱ ችግር” በሚል ርዕስ ባወጣው ዘገባ ላይ እንዲህ ብሏል:- “ከቀሳውስት መካከል ብዙዎች በአምላክ መኖር ወይም በረከትና ቅጣት አለ በሚለው መሠረተ ትምህርት ወይም በትንሣኤ አያምኑም። . . . ቀሳውስት ይህ ዓይነቱ አመለካከት ተጠናውቷቸዋል።”
ሌሎች አብያተ ክርስቲያናትም ተመሳሳይ ችግር ገጥሟቸዋል። በእንግሊዝ ቤተ ክርስቲያን ቄሰ ገበዞች ላይ የተካሄደ አንድ ጥናት አብዛኛዎቹ “ድንግል መውለዷን፣ ኢየሱስ ያደረጋቸውን ተአምራትና የመሲሑን ዳግም ምጽዓት በመሳሰሉ ሲወርዱ ሲዋረዱ በመጡ የክርስትና እምነት መሠረታዊ ገጽታዎች ላይ እምነት እንደሌላቸው” ማጋለጡን የአውስትራሊያው ካንቤራ ታይምስ ዘግቧል።
ሃይማኖት ነክ በሆኑ ጉዳዮች ላይ የሚጽፉት ጆርጅ አር ፕሌግነዝ አንድ ቄስ ራሱ የማያምንበትን ጸሎተ ሃይማኖት እንዲደግም ሕሊናው አንዴት ይፈቅድለታል ሲሉ ጠይቀዋል። አንድ ቄስ ጸሎተ ሃይማኖቱን በሚደግምበት ጊዜ “አምናለሁ” የሚለውን ቃል በሌላ ቃል እንደሚተካው ተናግሯል። “ጸሎተ ሃይማኖቱን በምደግምበት ጊዜ ‘ሁሉን ቻይ አምላክ በሆነው በአብ . . . ያምናሉ’ . . . እላለሁ” ሲል ተናግሯል። ፕሌግንዚ ይህ ዓይነቱን ግብዝነት “በዩናይትድ ስቴትስ ውስጥ የተፈጸመ ከባድ ሙስና” ብለው ጠርተውታል።
የሚያሳዝነው ይህን የመሰለው የቀሳውስት እምነት ማጣትና አታላይነት ብዙ ሰዎች ሃይማኖትን ባጠቃላይ እንዲጠራጠሩ ማድረጉ ነው። ሆኖም በዛሬው ጊዜ ሃይማኖትን በተመለከተ አሳሳቢ የሆነ ጉዳይ ይህ ብቻ አይደለም። አብዛኛዎቹ ቤተ ክርስቲያን ተሳላሚዎች መጽሐፍ ቅዱስ የአምላክ ቃል እንደሆነ ሲማሩ ኖረዋል። ሆኖም ከረጅም ዘመናት ጀምሮ ሲታመንባቸው የነበሩ አንዳንድ የቤተ ክርስቲያን መሠረተ ትምህርቶች መጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ እንደሌሉ ሲያውቁ ይደነቁ ይሆን? ቀጥሎ ያለው ርዕስ አንድ ምሳሌ ያቀርባል።