የአምላክ ስም ወደ ቀድሞ ቦታው ተመለሰ
“ይሖዋ የሚለው ስም ለብዙ ዓመታት ምናልባትም ለብዙ መቶ ዘመናት ከመጽሐፍ ቅዱስ ትርጉሞች እንዲወጣ ተደርጎ ከቆየ በኋላ ቴትራግራማተንን ወደ ቀድሞ ቦታቸው ለመመለስ ቆራጥ እርምጃ የወሰደ ብቸኛ የክርስትና ሃይማኖት ቢኖር ዘመናዊ ምሥክሮቹን ያቀፈው ሃይማኖት ነው።”a
ከላይ የተጠቀሰው አስተያየት የተወሰደው ብራዚላዊው ደራሲ አሲስ ብራዚል ጂኦቫ ዴንትሩ ዱ ጁዳዪዝሙ ኢ ዱ ክሪስቲያኒስሙ (ይሖዋ በአይሁድና በክርስትና ውስጥ) በሚል ርዕስ ከጻፉት መጽሐፍ ውስጥ ነው። ሆኖም ጥቂት የመጽሐፍ ቅዱስ ትርጉሞች በሆነ መንገድ በመለኮታዊው ስም ቢጠቀሙም ሌሎች ሃይማኖቶች ጨርሶ ከመጽሐፍ ቅዱስ ትርጉሞቻቸው ውስጥ ያስወጡት ለምንድን ነው? የሚለው ጥያቄ ሊነሳ ይችላል። “የአምላክን ስም ያስወጡት” ይላሉ ብራዚል፣ “ወይ በአጉል እምነት . . .፣ አሊያም ባላቸው ስውር ዓላማ ወይም ደግሞ የኢየሱስንና የእናቱን የማርያምን ስም ከፍ ከፍ ለማድረግ ካላቸው ምኞት የተነሣ ነው” ብለዋል።
ይሁን እንጂ ሚስተር ብራዚል በትክክል እንዳስቀመጡት:- “[መለኮታዊው] ስም በፖርቹጋል ቋንቋ በተዘጋጀው የአዲሲቱ ዓለም የቅዱሳን ጽሑፎች ትርጉም ላይ ሙሉ በሙሉ ተገቢ ወደሆነ ቦታው ተመልሷል።” እንዴት? በዚህ መጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ይሖዋ የሚለው ስም ወደ ቀድሞ ትክክለኛ ቦታው እንዲመለስ በመደረጉ ነው። ይሖዋ የሚለው ስም በአዲሲቱ ዓለም ትርጉም ውስጥ ከ7,200 ጊዜ በላይ ተጠቅሶ ይገኛል።
መጀመሪያ ታትሞ ከወጣበት ጊዜ አንስቶ በፖርቹጋል ቋንቋ የተዘጋጀው የዚህ ዘመናዊና ቀጥተኛ ትርጉም ስድስት ሚልዮን ተኩል ቅጂዎች ተሰራጭተዋል። በመሆኑም ዲአሪዩ ዱ ኖርዴስቲ (ኖርዝኢስተርን ዴይሊ) የተባለው በብራዚል ለሚታተም ጋዜጣ የሚጽፍ አንድ ጋዜጠኛ “አምላክ ስም እንዳለው ታውቁ ነበር?” ብሎ ለመጠየቅ ተገፋፍቶ ነበር። ለዚህ ዘመናዊ የመጽሐፍ ቅዱስ ትርጉም ምስጋና ይግባውና በአሁኑ ጊዜ በሚልዮን የሚቆጠሩ ሰዎች “አዎን። መለኮታዊው ስም ይሖዋ ነው” ብለው ለመመለስ ችለዋል።
[የግርጌ ማስታወሻ]
a በዕብራይስጥ ቋንቋ የአምላክ ስም ሲጻፍ יהוה ነው። (ከቀኝ ወደ ግራ የሚነበቡት) እነዚህ አራት ፊደላት በተለምዶ ቴትራግራማተን ተብለው ይጠራሉ።