የአምላክ ቃል ኃይል አለው
1 መጽሐፍ ቅዱስ በሚልዮን የሚቆጠሩ ሰዎችን ሕይወት በእጅጉ የለወጠ መጽሐፍ ነው። መልእክቱ የሰው ፈጠራ የሆነ ማንኛውም ነገር ሊያደርገው ከሚችለው በላቀ ሁኔታ አንድን ሰው ለመቀስቀስ ይችላል። (ዕብ. 4:12) ምን ያህል እንደጠቀመን እስቲ አስበው። ዋጋማነቱ ከምንም ነገር በላይ ነው።
2 ዋነኞቹ የመጽሐፍ ቅዱስ ተማሪዎችና ጠበቆች የይሖዋ ምሥክሮች ናቸው። የመጽሐፍ ቅዱስ ንባብ የመደበኛው ቲኦክራሲያዊ መርሐ ግብራችን ሊቀር የማይችል ክፍል እንደሆነ አድርገን ልንመለከተው ይገባናል፤ በተጨማሪም ቴሌቪዥን ከማየትና ከመሳሰሉት ሌሎች የጊዜ ማሳለፊያዎች የበለጠ ቅድሚያ ልንሰጠው ይገባል።
3 የዘወትር ልማድህ አድርገው፦ የይሖዋ ሕዝቦች አዘውትሮ መጽሐፍ ቅዱስ ማንበብ ሊያመጣ የሚችለውን ከፍተኛ ውጤት ተገንዝበዋል። በብሩክሊን ከሚገኙት ሕንፃዎቻችን በአንዱ ላይ ለአያሌ ዓመታት በትልቁ የተጻፈ አንድ ምልክት “የአምላክ ቃል የሆነውን መጽሐፍ ቅዱስ በየዕለቱ አንብቡ” ብሎ አላፊ አግዳሚውን ሲያበረታታ ቆይቷል። ከቤቴል ቤተሰብ ጋር የሚቀላቀሉ አዲስ አባላት በመጀመሪያው ዓመት የቤቴል አገልግሎታቸው መላውን መጽሐፍ ቅዱስ አንብበው እንዲጨርሱ ይፈለግባቸዋል። ፕሮግራምህ ምንም ያህል የተጣበበ ቢሆን በቲኦክራሲያዊ የአገልግሎት ትምህርት ቤት ፕሮግራም ላይ ለሳምንቱ ከቀረበው የመጽሐፍ ቅዱስ ንባብ ጋር እኩል እየተጓዝህ ነውን?
4 በዚህ ረገድ ችግር ካለብህ በኅዳር ወር ይህን ለማስተካከል ለምን አትጥርም? ለዚህ ወር በጠቅላላው የተሰጠው የመጽሐፍ ቅዱስ ንባብ ከመዝሙር 95–109 ድረስ ያለው ነው፤ ይህም በሳምንት ውስጥ የሚጠይቅብህ ሦስት ወይም አራት ገጾችን ማንበብ ነው። አንዳንዶች በየቀኑ ጠዋት ቀደም ብለው በመነሣት ወይም ማታ ከመኝታ በፊት ጥቂት ማንበብን መርጠዋል። ሆኖም በምንም መንገድ አድርገው ዋናው ነገር የአምላክን ቃል አዘውትሮ በማንበብ የሚገኘውን ሙሉ ጥቅም ማግኘትህ ነው።
5 ዛሬም ብዙ ሰዎች ለመጽሐፍ ቅዱስ አክብሮት አላቸው፤ ከዛ ስናነብላቸውም ለማዳመጥ እምቢ አይሉም። በኅዳር ወር የምናበረክተው መጽሐፍ ዛሬ ያሉ ወጣቶችና ወላጆች የሚገጥማቸውን ችግር ለመወጣት በአምላክ ቃል ውስጥ የሚገኘውን ጥበብ በሕይወታቸው እንዴት ሊሠሩበት እንደሚችሉ የሚጠቁማቸውን ወጣትነትህን በተሻለ መንገድ ተጠቀምበት የተባለውን መጽሐፍ ይሆናል። ይህ መጽሐፍ ልበ ቅን የሆኑ ሰዎች የመጽሐፍ ቅዱስን ዋጋማነት እንዲመለከቱ ለማድረግ ግሩም አጋጣሚ ይሰጣቸዋል። ይህን መጽሐፍ ስታበረክት ሞቅ ባለ ስሜት ተናገር።
6 ወጣትነትህ የተባለውን መጽሐፍ እንዲወስዱ የሰዎችን ፍላጎት ሊያነሣሱ የሚችሉ በደንብ የታሰበባቸውን ነጥቦች ጎላ ካሉት የመጽሐፉ ክፍሎች አዘጋጅ። የመጽሐፉን ተግባራዊነት ጎላ አድርገህ ግለጽላቸው። በ“መጽሐፍ ቅዱሳዊ የውይይት አርዕስት” ላይ ከተገለጹት ርዕሶች በአንዱ ልትጠቀም ትችል ይሆናል። ይህንንም ከመጽሐፉ ጋር አዛምደህ አቅርበው። ለምሳሌ “ጋብቻ” በሚለው ርዕስ ሥር (38 መ) “ክርስቲያን ወላጆች ለልጆቻቸው ያላቸው ኃላፊነት” የሚለውን ልትጠቀም ትችላለህ፤ በዚህም ርዕስ ሥር 2 ቆሮንቶስ 12:14፤ 1 ጢሞቴዎስ 5:8፤ ኤፌሶን 6:4፤ ምሳሌ 22:6, 15 እና ምሳሌ 23:13, 14 የመሳሰሉት የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅሶች ተካትተዋል።
7 አዎን፣ መጽሐፍ ቅዱስ የአምላክ ቃል ነው። ካነበበነው፣ ካመንንበት እና የሚሰጠንን ምክር በሕይወታችን ውስጥ ከሠራንበት፣ ታላቅ በረከት እናጭዳለን። መመሪያና ተስፋንም ይሰጠን ዘንድ የተጻፈ ነው። (ሮሜ 15:4) በየዕለቱ ቃሉን መመልከታችንና በርሱ ተጠቅመን ሌሎችን ለማስተማር ዝግጁ መሆናችን የግድ አስፈላጊ ነው።