ለሌሎች አሳቢነትን አሳዩ— ክፍል 1
1 ብዙ ጉባኤዎች እንዲቋቋሙ ያስቻለውን የይሖዋ ሕዝቦች ብልጽግና ስናይ እንደሰታለን። በአንዳንድ ቦታዎች በተለይም በትልልቅ ከተማዎች አካባቢ አንዳንዴ ከአንድ በላይ ጉባኤዎች በአንድ የመንግሥት አዳራሽ እንዲጠቀሙ የሚያስገድድ የመንግሥት አዳራሽ ሕንፃዎች እጦት አለ። ይህ ሁኔታ የሚመለከታቸው ሁሉ ከወትሮው የበለጠ አሳቢነት እንዲያሳዩ ይፈለግባቸዋል።
2 የመንግሥት አዳራሹን የሚጠቀም እያንዳንዱ ጉባኤ ቀጥሎ ለሚመጡት ወንድሞች ንጹሕና ሥርዓታማ በሆነ መንገድ ማስረከብ ይኖርበታል። ወንበሮቹ በሥርዓት መደርደር፣ በጽሑፍ መሸጪያው ጠረጴዛ ላይ ያሉ ጽሑፎች በሙሉ በተገቢ ቦታቸው መቀመጥና በመንግሥት አዳራሹ ውስጥ በየቦታው ተዝረክርከው የሚታዩ የግል ንብረቶች ሁሉ መሰብሰብ አለባቸው። ሳሙና፣ ፎጣዎችና የሽንት ቤት ወረቀቶች መቀየራቸውንና የቆሻሻ ማጠራቀሚያዎች መጋባታቸውን በማረጋገጥ ሽንት ቤቱን በንጹሕ ሁኔታ ማስረከብ ይገባል።
3 ከአጭር ጊዜ በኋላ የሚጀመር ሌላ ስብሰባ ካለ ከመጀመሪያው ስብሰባ በኋላ የሚቆዩ ለቀጣዩ ስብሰባ የሚደረገውን ዝግጅት ስለሚያደናቅፉ ሳያስፈልግ መዘግየት የለባቸውም። የደራ የግል ጭውውት በበሩ አካባቢ ጭንቅንቅ ሊፈጥርና ወንድሞች ለቀጣዩ ስብስባ ነገሮችን እንዳያደራጁ ሊያዘገያቸው ይችላል። በመንግሥት አዳራሹ አካባቢ ያለው የመኪና ማቆሚያ መጠነኛ ሊሆን ይችላል፤ ስለዚህ ለሚመጡ የመኪና መቆሚያ ቦታ ለመልቀቅ ቶሎ መውጣት ደግነት ይሆናል። በሌላ በኩል ቀጣዩን ስብስባ የሚያደርጉ የማያስፈልግ መጨናነቅ እንዳይፈጠር ከሰዓቱ ብዙ ቀድመው መምጣት የለባቸውም።
4 ከአንድ በላይ ጉባኤዎች በሚሰበሰቡበት ወቅት በየሳምንቱ የመንግሥት አዳራሹን ለማጽዳት ዝግጅት በማድረግ በኩል ተቀራርቦ መሥራት ልዩ ትኩረት ይጠይቃል። አብዛኛውን ጊዜ ጉባኤዎች ለተወሰነ ጊዜ ተራ ይገባሉ። የእናንተ ጉባኤ ይህን ኃላፊነት ሲረከብ ጽዳቱ በወቅቱ በደንብ እንደተከናወነ አረጋግጡ። እንዲህ ካደረጋችሁ ሌሎች በአዳራሹ የሚጠቀሙ ጉባኤዎች የሚማረሩበት ምክንያት አይኖርም።
5 አልፎ አልፎ እንደ የክልል የበላይ ተመልካች ጉብኝት ባሉ ጊዜያት እያንዳንዱ ጉባኤ የሚሰበሰብበትን ሰዓት መቀየር ያስፈልገው ይሆናል። ለውጡ ሌላ ጉባኤን የሚነካ ከሆነ ሽማግሌዎች በተቻለ መጠን ቀደም ብለው ለአስፋፊዎቹ ማሳወቅ እንዲችሉ ከተወሰነ ጊዜ በፊት ጉዳዩ ለሚመለከተው ጉባኤ መንገር አለባቸው። በተጨማሪም እንደ የአቅኚነት አገልግሎት ትምህርት ቤት፣ የክልሉ ሽማግሌዎች ስብሰባ ወይም ሠርግ ያለ የተፈቀደ ተግባር ለማከናወን ፕሮግራም ተይዞ ከሆነ ሌሎች ጉባኤዎችና ጉዳዩ የሚመለከታቸው የክልል የበላይ ተመልካቾች በቅድሚያ ሊነገራቸው ይገባል፤ እንደዚህ መደረጉ በተመሳሳይ ሰዓት የመንግሥት አዳራሹን ለመጠቀም ፕሮግራም እንዳያወጡ ያደርጋል።
6 ለሌሎች ፍቅራዊ አሳቢነት ማሳየት፣ ጥሩ የሐሳብ ግንኙነት ማድርግ፣ በቅድሚያ እቅድ ማውጣትና እርስ በርስ መተባበር በጉባኤዎች መካከል ያለውን ሞቅ ያለ ግንኙነት ሊጠብቅና ‘ሁሉ በአግባብና በሥርዓት እንዲሆን’ ሊያደርግ ይችላል።— 1 ቆሮ. 14:40