ሁሉም ዓይነት ሰዎች ይድናሉ
1 የይሖዋ ፈቃድ “ሁሉም ዓይነት ሰዎች እንዲድኑና ትክክለኛውን የእውነት እውቀት ወደማወቅ እንዲደርሱ ነው።” (1 ጢሞ. 2:4 NW ) ምንም እንኳ ሰዎች ዘራቸው፣ አስተዳደጋቸውና ከአካባቢያቸው የወረሷቸው ነገሮች በከፊል ተጽዕኖ ሊያሳድሩባቸው ቢችሉም ሕይወታቸውን እንዴት እንደሚጠቀሙበት በግል የመምረጥ ነፃነት አላቸው። ጥሩ የሆነውን አድርገው በሕይወት ሊኖሩ አለዚያም መጥፎ የሆነውን ነገር አድርገው ሊጠፉ ይችላሉ። (ማቴ. 7:13, 14) ይህ ግንዛቤ የመንግሥቱን ምሥራች ለምንነግራቸው ሰዎች ያለንን አመለካከት የሚነካው እንዴት ነው?
2 አንድ ሰው ለእውነት የሚያሳድረው ፍላጎት በትውልድ አገሩ ወይም በባሕሉ ወይም በኅብረተሰቡ ውስጥ ባለው ቦታ ላይ የተመካ ነው ብለን ማሰብ አይኖርብንም። እውነት ከፍተኛም ሆነ አነስተኛ የትምህርት ደረጃ ያላቸው ሰዎችን፣ በፖለቲካ ውስጥ ንቁ ተሳትፎ የሚያደርጉትን፣ በአምላክ መኖር የማያምኑትን፣ ስለ አምላክ ምንም ማወቅ አይቻልም የሚሉትንና አገር ያሰለቹ ወንጀለኞችን እንኳን ሳይቀር ሊማርክ ይችላል። የተለያየ ዓይነት አስተዳደግና የተለያየ ዓይነት የኑሮ ደረጃ ያላቸው ሰዎች ከቀድሞ የአኗኗር መንገዳቸው ለውጥ አድርገው በአሁኑ ጊዜ ወደ አዲስ ዓለም በሚያስገባው ጎዳና ላይ በመጓዝ ላይ ናቸው። (ምሳሌ 11:19) ስለዚህ የመንግሥቱን መልእክት የተለያየ የአኗኗር መንገድ ወዳላቸው ሰዎች ይዘን ለመሄድ ማመንታት አይኖርብንም።
3 እነዚህን ምሳሌዎች ተመልከቱ:- አንድ ሰው የእንጀራ አባቱን ለመግደል ያስብና ይተወዋል። ከዚያም ራሱን ለመግደል ቢወስንም እንደዚያ ማድረግ ሳይችል ይቀራል። በሌብነትና አደንዛዥ ዕፅ በማዘዋወር ወንጀል ከታሰረ በኋላ ትዳሩ ፈረሰ። በአሁኑ ጊዜ ይህ ሰው የሃቀኝነት ኑሮ እየኖረና ደስተኛ ቤተሰብ የመሠረተ ከመሆኑም በላይ ከእንጀራ አባቱ ጋር ጥሩ ግንኙነት አለው። እንዲህ ያለውን ለውጥ እንዲያደርግ የረዳው ምንድን ነው? ከይሖዋ ምሥክሮች ጋር መጽሐፍ ቅዱስን በማጥናቱና የተማራቸውን ነገሮች በሥራ ላይ በማዋሉ ነው። ይሖዋ ይህ ሰው በክርስቶስ መሥዋዕት ሊቤዥ አይችልም ብሎ አላሰበም።
4 አንዲት ሴት ታዋቂ የቴሌቪዥን ተዋናይ መሆኗ ምንም ዓይነት ደስታ አላስገኘላትም ነበር። ይሁን እንጂ ምሥክሮቹ ያላቸውን ንጹሕ ሥነ ምግባር አይታ በመደነቋ መጽሐፍ ቅዱስን ማጥናት ጀመረች። ብዙ ሳይቆይ ሌሎች የመንግሥቱን ምሥራች እንዲያውቁ መርዳት ጀመረች። ከቤት ወደ ቤት ስትሄድ የምታገኛቸው ሰዎች ሁሉ ያስታውሷታል። እርሷ ግን እንደ አንዲት ተዋናይ ሆና ከመታወቅ ይልቅ እንደ አንዲት የይሖዋ ምሥክር ሆና መታወቅ እንደምትፈልግ በደስታ ትገልጻለች።
5 አንዲት የይሖዋ ምሥክር የመጠበቂያ ግንብ ኮንትራት የገባችን ሴት መጽሐፍ ቅዱስ ለማስጠናት በምታነጋግራት ጊዜ አንዲት ጎረቤት ሰማችና በጥናቱ ላይ ተገኘች። ጎረቤትየዋ ለረዥም ጊዜ ትፈልገው የነበረውን እውነት እንዳገኘች ወዲያው ተገነዘበች! እርሷና ባሏ እንዲፈርስ የጸደቀውን ጋብቻቸውን ሰርዘው እንደገና በሰላም መኖር ጀመሩ። ይህቺ ሴት በኮከብ ቆጠራ ተጠላልፋ የነበረች ሲሆን በመናፍስት አምልኮም ትካፈል ነበር። ይሁን እንጂ ከአጋንንታዊ አምልኮ ጋር ግንኙነት ያላቸውን ውድ የሆኑ መጽሐፎችንና ሌሎች ዕቃዎችን ሁሉ አስወገደች። ብዙም ሳይቆይ በስብሰባ ላይ መገኘት፣ ለዘመዶቿና ለጓደኞቿም ስለ አዲስ እምነቷ መናገር ጀመረች። በአሁኑ ጊዜ ለሌሎች በጋለ ስሜት በመመሥከር ላይ ነች።
6 በማንም ሰው ላይ መጥፎ አስተያየት ሊኖረን አይገባም። ከዚህ ይልቅ ምሥራቹን በየትም ቦታ ለሚኖሩ ሰዎች በቅንዓት እናካፍላቸው። ‘ልብን ማየት’ የሚችለው ይሖዋ “ሁሉንም ዓይነት ሰዎች የሚያድን” መሆኑን ለማመን የሚያስችል ብዙ ምክንያቶች አሉን።— 1 ሳሙ. 16:7፤ 1 ጢሞ. 4:10 NW