የበለጠ ማድረግ እንችላለን
1 ኢየሱስ ክርስቶስ በአገልግሎቱ ድንቅ ሥራዎችን አከናውኖ ነበር። በሺህ የሚቆጠሩ ሰዎችን በተአምር መግቧል፣ በርካታ ሰዎችን ፈውሷል እንዲሁም ጥቂት ሰዎችን ከሞት አስነስቷል። (ማቴ. 8:1-17፤ 14:14-21፤ ዮሐ. 11:38-44) ያከናወናቸው ነገሮች የመላውን ብሔር ትኩረት ስቧል። ሆኖም ከመሞቱ በፊት በነበረው የመጨረሻ ምሽት ለታማኝ ተከታዮቹ የሚከተለውን ተናገረ:- “እውነት እውነት እላችኋለሁ፣ በእኔ የሚያምን እኔ የማደርገውን ሥራ እርሱ ደግሞ ያደርጋል፤ ከዚህም የሚበልጥ ያደርጋል።” (ዮሐ. 14:12) “የሚበልጥ” ሥራ ልንሠራ የምንችለው እንዴት ነው?
2 ይበልጥ ሰፊ ክልል በመሸፈን፦ የኢየሱስ የእንቅስቃሴ አድማስ በፍልስጥኤም ምድር ብቻ የተወነሰ ሲሆን ለመጀመሪያዎቹ ደቀ መዛሙርቱ ግን ‘እስከ ምድር ዳር ድረስ’ ማለትም ኢየሱስ ካከናወነው ስብከት ይበልጥ ስፋት ባለው መጠን እንደሚመሰክሩ ነግሯቸው ነበር። (ሥራ 1:8) ኢየሱስ የጀመረው የስብከት ሥራ በአሁኑ ጊዜ 232 አገሮችን የሚያቅፍ ዓለም አቀፋዊ ይዘት ያለው ሥራ ሆኗል። (ማቴ. 24:14) ለጉባኤህ በተመደበው የአገልግሎት ክልል ውስጥ በመሥራት የበኩልህን አስተዋጽኦ እያበረከትክ ነው?
3 ብዙ ሰዎችን በማነጋገር፦ የስብከቱን ሥራ ከኢየሱስ የተረከቡት ደቀ መዛሙርት ቁጥር በአንጻራዊ ሁኔታ ሲታይ በጣም ጥቂት ነበር። ይሁን እንጂ በ33 እዘአ በዋለው የጰንጤቆስጤ ዕለት ባከናወኑት ቅንዓት የተሞላበት ስብከት በዚያው ዕለት ወደ ሦስት ሺህ የሚጠጉ ነፍሳት እውነትን ተቀብለው ሊጠመቁ ችለዋል። (ሥራ 2:1-11, 37-41) ‘ለዘላለም ሕይወት ዝንባሌ ያላቸውን’ ሰዎች የመሰብሰቡ ሥራ እስከ ጊዜያችንም ድረስ የቀጠለ ሲሆን ዛሬ በየቀኑ በአማካይ ከ1,000 የሚበልጡ ሰዎች ይጠመቃሉ። (ሥራ 13:48 NW) ቅን ልብ ያላቸውን ሰዎች በሚገኙበት ቦታ ሁሉ ለመፈለግና ፍላጎት ያሳዩትን ሰዎች በተቻለ ፍጥነት ተከታትለህ ለመርዳት አቅምህ የፈቀደልህን ሁሉ በማድረግ ላይ ነህን?
4 ረዘም ላለ ጊዜ በመስበክ፦ ኢየሱስ በምድር ላይ አገልግሎቱን ያከናወነው ለሦስት ዓመት ተኩል ብቻ ነበር። አብዛኞቻችን ከዚህ ለሚበልጡ ዓመታት ሰብከናል። ይህን ሥራ ለመሥራት የሚፈቀድልን ጊዜ የቱንም ያክል ይሁን የቱን እያንዳንዱ አዲስ ደቀ መዝሙር ወደ ሕይወት በሚያደርሰው ጎዳና ላይ መጓዝ እንዲጀምር የመርዳት መብት በማግኘታችን አመስጋኞች ነን። (ማቴ. 7:14) በየወሩ የጌታ ሥራ የበዛልህ ነህን?—1 ቆሮ. 15:58
5 የኢየሱስ እውነተኛ ደቀ መዛሙርት እንደመሆናችን መጠን እርሱ በሚሰጠን ድጋፍ ገና ከዚህ የበለጡ ሥራዎችን ማከናወን እንደምንችል እርግጠኞች ልንሆን እንችላለን።—ማቴ. 28:19, 20