‘መልካሙን የእምነት ገድል ተጋደሉ’
1 ሐዋርያው ጳውሎስ ጢሞቴዎስን “መልካሙን የእምነት ገድል ተጋደል” ሲል አጥብቆ መክሮታል። (1 ጢሞ. 6:12) ጳውሎስ ራሱም ከእነዚህ ቃላት ጋር በሚስማማ መንገድ ኖሯል። በሕይወቱ ማብቂያ አካባቢ በበኩሉ መልካሙን ገድል እንደተጋደለ በእርግጠኝነት መናገር ችሎ ነበር። (2 ጢሞ. 4:6-8) ጳውሎስ በማንኛውም ሁኔታ ሥር አገልግሎቱን በድፍረት፣ በቆራጥነትና በጽናት ፈጽሟል። እኛም የእርሱን ምሳሌ በመከተል ለክርስቲያናዊ እምነታችን በምናደርገው ተጋድሎ አቅማችን የሚፈቅደውን ሁሉ እያደረግን እንዳለን ሙሉ ትምክህት ሊያድርብን ይችላል።
2 አስፈላጊውን ጥረት አድርጉ:- ጳውሎስ አገልግሎቱን ለመፈጸም ከፍተኛ ጥረት አድርጓል። (1 ቆሮ. 15:10) እኛም በክልላችን ውስጥ የሚገባቸውን ሰዎች ፈልገን ለማግኘት ጥረት ማድረግ ይኖርብናል። (ማቴ. 10:11) ከእነዚህም መካከል አንዳንዶቹን ለማግኘት ጠዋት ቀደም ብሎ በመነሳት መንገድ ላይ መመሥከር ሊጠይቅ ይችላል። ወይም ደግሞ ወደ ቤታቸው የተመለሱትን ሰዎች ለማግኘት በቀኑ መገባደጃ ላይ ወይም አመሻሹ ላይ መሥራት ይኖርብን ይሆናል።
3 ከመጽሐፍ ጥናት ቡድናችን ጋር ለምናደርገው የመስክ ስምሪት ስብሰባ በሰዓቱ መድረስ ራስን መግዛትና ጥሩ ፕሮግራም ማውጣት ይጠይቃል። ለምሳሌ፣ አንዳንድ የቤቴል ቤተሰብ አባላት በሳምንቱ መጨረሻ ላይ በተመደቡባቸው ጉባኤዎች በአገልግሎት ለመካፈል ወደ ቦታው ለመድረስ ብቻ ወደ አንድ ሰዓት ገደማ ይጓዛሉ። ከዚህም በተጨማሪ ረዥም ጉዞ ማድረግ ቢጠይቅባቸውም ልክ በሰዓቱ የሚደርሱትን አንዳንድ የጉባኤያችንን አስፋፊዎችና ቤተሰቦች እናደንቅ ይሆናል። ትጉዎች በመሆንና በሚገባ በመደራጀት ረገድ እያሳዩት ያለው ምሳሌ በእርግጥም ሊኮረጅ ይገባዋል።
4 የምናገኛቸውን ፍላጎት ያሳዩ ሰዎች ሁሉ ተከታትለን ለመርዳት መገፋፋት ይኖርብናል። በመንገድ ላይ ወይም መደበኛ ባልሆነ መንገድ በመመሥከር ጽሑፍ ያበረከትንለትን ሰው አድራሻ ወይም ስልክ ቁጥር ለማግኘት መጣር ይኖርብናል። ከዚያም ሰውዬውን በማነጋገር ፍላጎቱን ማሳደግና የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት እንዲጀምር ጥረት ማድረግ እንችላለን።
5 በአገልግሎቱ አዘውታሪዎች ሁኑ:- ጳውሎስ የስብከቱን ሥራ ሙሉ በሙሉ ለመፈጸም ያልተቋረጠ ጥረት አድርጓል። (ሮሜ 15:19) እናንተስ? በአገልግሎቱ አዘውትራችሁ ትካፈላላችሁ? እስከ አሁንስ በዚህ ወር በአገልግሎት ተካፍላችኋል? የመጽሐፍ ጥናት ቡድን መሪዎች በቡድናቸው ውስጥ የሚገኙት ሁሉም አስፋፊዎች በነሐሴ ወር በአገልግሎት ሲካፈሉ ማየት ይፈልጋሉ። እንዲህ ማድረግ ትችሉ ዘንድ ይረዷችኋል።
6 ጳውሎስ ምሥራቹን ሙሉ በሙሉ በመደገፍ ረገድ ያሳየውን ምሳሌ በመኮረጅ ‘መልካሙን የእምነት ገድል መጋደላችንን’ እንቀጥላለን።