እንደ ጥበበኞች ኑሩ
1 ኢየሱስ አራት ዓሣ አጥማጆችን የእሱ ተከታዮች እንዲሆኑ በጠየቃቸው ጊዜ ውሳኔ ለማድረግ አላመነቱም፤ ከዚያ ይልቅ “ወዲያው . . . ተከተሉት።” (ማቴ. 4:18-22) የጠርሴሱ ሳውልም በተመሳሳይ ወደ ክርስትና ከተለወጠና የማየት ችሎታው ከተመለሰለት በኋላ እርምጃ ለመውሰድ ዛሬ ነገ ከማለት ይልቅ “ወዲያውም፣ ኢየሱስ የእግዚአብሔር ልጅ መሆኑን በየምኵራቦቹ መስበክ ጀመረ።” (ሥራ 9:20) ጊዜ ያለማቋረጥ ወደፊት ይነጉዳል፤ አንዴ ካለፈ ደግሞ ተመልሶ አይገኝም። በጊዜ አጠቃቀማችን ረገድ ‘እንደ ጥበበኞች መኖራችን’ አስፈላጊ የሆነው ለዚህ ነው።—ኤፌ. 5:15, 16
2 ያልታሰበ አጋጣሚ:- ዛሬ ይሖዋን ለማገልገል ያለንን አጋጣሚ ነገ ላናገኘው እንችላለን። (ያዕ. 4:14) “ያልታሰበ አጋጣሚ” ከሚያመጣው ነገር ማንም ሰው ማምለጥ አይችልም። (መክ. 9:11 NW) በተጨማሪም ሁላችንም በዕድሜ እየገፋን መሄዳችን አይቀርም። በዚህ ሥርዓት ውስጥ እስካለን ድረስ ከዕድሜ መግፋት ጋር ተያይዞ ከሚመጣውና በይሖዋ አገልግሎት የፈለግነውን ያህል ማከናወን እንዳንችል አቅማችንን ከሚገድብብን “የጭንቀት ጊዜ” ማምለጥ አንችልም። (መክ. 12:1) በመሆኑም ራሳችንን ለአምላክ ለመወሰን ማመንታት አይኖርብንም። እንዲሁም በአሁኑ ጊዜ የምንችለውን ያህል አገልግሎታችንን ከማስፋት ይልቅ ሁኔታዎች እስኪመቻቹ ድረስ መጠበቃችን ጥበብ አይደለም። (ሉቃስ 9:59-62) አብርሃም በኋለኞቹ ዓመታት ሰላም አግኝቶና “ዕድሜ ጠግቦ በመልካም ሽምግልና” የሞተው ሙሉ በሙሉ ለይሖዋ ያደረ በመሆን ሕይወቱን በጥበብ ስለተጠቀመበት ነው።—ዘፍ. 25:8
3 ዘመኑ አጭር ነው:- ጊዜያችንን በጥበብ መጠቀም የምንፈልግበት ሌላው ምክንያት ደግሞ “ዘመኑ አጭር” መሆኑ ነው። (1 ቆሮ. 7:29-31) በቅርቡ ይህ አሮጌ ሥርዓት ይደመደማል። “የምድር መከር” የሚሰበሰብበት ይህ ጊዜ ካበቃ በኋላ በግ መሰል ሰዎችን በመሰብሰቡ ታላቅ ሥራ ለመካፈል የሚያስችል ሌላ አጋጣሚ አይኖረንም። (ራእይ 14:15) የኑሮ ጭንቀቶችና ሐሳብን የሚከፋፍሉ ነገሮች በአገልግሎት ልናሳልፈው የሚገባውን ጊዜ እንዲሻሙብን መፍቀድ አይኖርብንም። (ሉቃስ 21:34, 35) ወደኋላ መለስ ብለን ስንመለከት በመከሩ ሥራ ሙሉ ተሳትፎ አድርገን እንደነበረ ማወቅ እንዴት የሚያስደስት ይሆናል!
4 ከፊታችን በሚዘረጉ አስደሳች የአገልግሎት መብቶች የመካፈል አጋጣሚ እንዳያመልጠን ዘወትር ንቁዎች ልንሆን ይገባናል። ይሖዋን ‘ዛሬውኑ’ ለማገልገል የቻልነውን ሁሉ ማድረግ ቁርጥ ውሳኔያችን ይሁን። (ዕብ. 3:13) እንደዚህ ማድረጋችን በእርግጥም ጥበበኞች መሆናችንን ያሳያል፤ ምክንያቱም መጽሐፍ ቅዱስ “የእግዚአብሔርን ፈቃድ የሚፈጽም ግን ለዘላለም ይኖራል” በማለት ይናገራል።—1 ዮሐ. 2:17