ለሌሎች የምናካፍለው ውድ ሀብት አለን
1 የአምላክ ቃል ከፍ አድርገን በምንመለከታቸው በርካታ መንፈሳዊ ሀብቶች የተሞላ ነው። (መዝ. 12:6፤ 119:11, 14) በአንድ ወቅት ኢየሱስ የመንግሥቱን የተለያዩ ገጽታዎች የሚያሳዩ ምሳሌዎችን ከተናገረ በኋላ ደቀ መዛሙርቱን “የዚህ ሁሉ ትርጉም ገብቷችኋል?” ብሎ ጠይቋቸው ነበር። “አዎን” የሚል መልስ ሲሰጡት “ስለዚህም የመንግሥተ ሰማይን ምስጢር የተረዳ ማንኛውም የኦሪት ሕግ መምህር፣ ከከበረ ሀብቱ ክምችት አዲሱንም አሮጌውንም የሚያወጣ ባለንብረት ይመስላል” አላቸው።—ማቴ. 13:1-52
2 መጽሐፍ ቅዱስን ማጥናት በጀመርንበት ጊዜ የተማርናቸው እውነቶች እንደ አሮጌ ሀብት ሊታዩ ይችላሉ። በየጊዜው በምናደርገው የግል ጥናት አማካኝነት በአምላክ ቃል ውስጥ የሚገኙትን ጥልቅ ነገሮች እየተረዳን ስንሄድ ደግሞ ሌሎች የመጽሐፍ ቅዱስ እውነቶችን እናገኛለን፤ እነዚህ እውነቶች ለእኛ እንደ አዲስ ሀብት ናቸው። (1 ቆሮ. 2:7) በተጨማሪም “ታማኝና ልባም ባሪያ” እንደ ውድ ሀብት የምንቆጥራቸውን አዳዲስ እውነቶች ያስተምረናል።—ማቴ. 24:45 የ1954 ትርጉም
3 አሮጌዎቹንም ሆነ አዲሶቹን መንፈሳዊ ሀብቶች ከፍ አድርገን እንመለከታቸዋለን። ይህም የአምላክ ቃል አስተማሪዎች እንደመሆናችን መጠን የተማርናቸውን ውድ እውነቶች ለሌሎች በልግስና ማካፈል እንድንችል አስፈላጊውን ሥልጠና ለመውሰድ ብሎም ተሞክሮ ለማካበት ጥረት እንድናደርግ ያነሳሳናል።
4 ኢየሱስ ምን ምሳሌ ትቷል? ኢየሱስ እነዚህን ውድ ሀብቶች ከፍ አድርጎ ይመለከት ስለነበር ለሌሎች ለማካፈል ከፍተኛ ጥረት አድርጓል። ድካም ተጫጭኖት በነበረበት ጊዜም እንኳ እነዚህን ውድ ሀብቶች ‘ከማከማቻው’ ማውጣቱን አላቆመም።—ዮሐ. 4:6-14
5 ኢየሱስ በመንፈሳዊ ድሆች ለሆኑ ሰዎች የነበረው ፍቅር በአምላክ ቃል ውስጥ ያለውን ሕይወት የሚያስገኝ ውድ ሀብት እንዲያካፍል አነሳስቶታል። (መዝ. 72:13) በመንፈሳዊ ለተራቡ ሰዎች ያዝን ስለነበር ‘ብዙ ነገር አስተምሯቸዋል።’—ማር. 6:34
6 ኢየሱስን ኮርጁ፦ ያለንን ውድ ሀብት ከፍ አድርገን የምንመለከት ከሆነ እኛም እንደ ኢየሱስ መንፈሳዊ ዕንቁዎችን በቀጥታ ከመጽሐፍ ቅዱስ ላይ ለሰዎች ለማሳየት እንጓጓለን። (ምሳሌ 2:1-5) አንዳንድ ጊዜ ሊደክመን ቢችልም እንኳ የመጽሐፍ ቅዱስን እውነቶች ከልብ በመነጨ ስሜት እንናገራለን። (ማር. 6:34) ውድ ለሆነው ሀብታችን ያለን ከፍተኛ አድናቆት ዘወትር በአገልግሎት የተሟላ ተሳትፎ ለማድረግ የተቻለንን ሁሉ ጥረት እንድናደርግ ይገፋፋናል።