ጵጵስናን ያቋቋመው ክርስቶስ ነውን?
“በመጀመሪያው የሮም ጳጳስ በጴጥሮስና ባሁኑ ጳጳስ በዮሐንስ ጳውሎስ 2ኛ መሐል ከ260 የሚበልጡ ሊቃነ ጳጳሳት አልፈዋል።” ይህን ያሉት ካቶሊኩ ፍራየር እቶኢ ፎይ በደቡብ አፍሪካው ደቡባዊ መስቀል በተሰኘ የካቶሊክ ሣምንታዊ መጽሔት ላይ ነው። በመቀጠልም እንዲህ ብለዋል፦ “የካቶሊክ ቤተክርስቲያን በኢየሱስ ክርስቶስ የተመሠረተ ለመሆኑ ማስረጃ ስንጠየቅ ወደዚህ ያልተቋረጠ ተከታታይ የመንበረ ጳጳሳት መሥመር በኩራት እናመለክታለን።”
ረዥሙ የጳጳሳት መሥመር የጀመረው በእርግጠኝነት ሊነገር ይችላልን? በካቶሊክ ሃይማኖታዊ ትምህርት መሠረት አራት ጳጳሳት ማለትም ሊኖስ፣ አናክሌተስ፣ ክሌመንት 1ኛና ኢቫሪስተስ ከጴጥሮስ በኋላ እስከ 100 እዘአ ድረስ በመተካት ሠርተዋል ይባላል። መጽሐፍ ቅዱስ በሮም ይኖር የነበረ ሊኖስ የሚባል ክርስቲያን እንደነበረ ይጠቅሳል። (2 ጢሞቴዎስ 4:21) ይሁን እንጂ ሊኖስ ወይም ሌላ ሰው ጴጥሮስን በጳጳስነት ተክቶታል ለማለት የሚያስችል ምንም ማስረጃ የለም። በመጀመሪያው መቶ ዘመን መጨረሻ ላይ አምስቱን የመጽሐፍ ቅዱስ መጻሕፍት የጻፈው ሐዋርያው ዮሐንስ ጴጥሮስን ተክተውታል ስለተባሉት ከላይ የተገለጹ ሰዎች ምንም የጠቀሰው ነገር የለም። በእርግጥ ጴጥሮስ ተተኪ ከኖረው ሊመርጥ የሚገባው ዮሐንስ ራሱ አይሆንም ነበርን?
ጴጥሮስ የሮም የመጀመሪያ ጳጳስ ነበር ስለመባሉ እሱ የሮምን ከተማ ስለመጎብኘቱም ወይም ሮምን አይቶ ስለማወቁም እንኳ ቢሆን ማስረጃ የለም። እንዲያውም ጴጥሮስ ራሱ የመጀመሪያውን ደብዳቤ የጻፈው ባቢሎን ሆኖ እንደነበረ ይናገራል። (1 ጴጥሮስ 5:13) ጴጥሮስ “ባቢሎን” የሚለውን ስም የተጠቀመበት ሮምን በሚሥጥር (በውስጠ ታዋቂ) ለመጥቀስ ነው የምትለው የካቶሊክ ቤተክርስቲያን መከራከሪያ መሠረተ ቢስ ነው። እውነተኛዋ ባቢሎን በጴጥሮስ ዘመን ነበረች። በተጨማሪም ባቢሎን በወቅቱ በርከት ያሉ የአይሁድ ሕዝብ የሚኖሩባት ከተማ ነበረች። ኢየሱስ ጴጥሮስን ስብከቱ በተገረዙ አይሁድ ላይ እንዲያተኩር መድቦት ስለነበር ጴጥሮስ ለዚሁ ዓላማ ባቢሎንን ጎብኝቷታል ብሎ ማመን ምክንያታዊ ነው።—ገላትያ 2:9
ጴጥሮስ ራሱን ከክርስቶስ ሐዋርያት እንደ አንዱ እንጂ ከዚያ በላይ እንደሆነ ጠቅሶ እንደማያውቅም አስተውል። (2 ጴጥሮስ 1:1) በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ጴጥሮስ “ቅዱስ አባት” “ከፍተኛ ጳጳስ” ወይም “ጳጳስ ”(በላቲንኛ ፓፓ “አባት” ለማለት የፍቅርና የቁልምጫ አጠራር) ተብሎ የተጠቀሰበት ቦታ የትም አይገኝም። ከዚህ ይልቅ ኢየሱስ በማቴዎስ 23:9,10 ላይ የተናገራቸውን ቃላት በጥብቅ ተከትሏል፦ “አባታችሁ አንዱ እርሱም የሰማዩ ነውና በምድር ላይ ማንንም አባት ብላችሁ አትጥሩ። ሊቃችሁ (መሪያችሁ) አንድ እርሱም ክርስቶስ ነውና ሊቃውንት ተብላችሁ አትጠሩ።” ጴጥሮስ አምልኮታዊ ክብር አልተቀበለም። ሮማዊው መቶ አለቃ ቆርኔሌዎስ “ሊሰግድለት ከእግሩ በታች ሲወድቅ፦ ተነሣ እኔ ራሴ ደግሞ ሰው ነኝ ብሎ አስነሥቶታል።”—ሥራ 10:25,26
260 ጳጳሶች ነበሩ ስለሚባሉት፤ ቄስ ፎይ፦ “በርካታዎቹ ለከፍተኛ ሥልጣናቸው የማይበቁ ነበሩ” በማለት አምነዋል። አዲሱ የካቶሊክ ኢንሳይክሎፔዲያ እንዲህ መሆኑ ቅር የማያሰኝ መሆኑን ሲገልጽ “በአስተዳደር በኩል ትልቅ ግምት የሚሰጠው የያዘው የስልጣን ቦታ ነው እንጂ የግለሰብ ጳጳሱ የግል ጠባይ አይደለም። ጳጳሱ በጠባዩ ቅዱስ ሊሆን ይችላል፤ ወይም እዚህ ግባ የማይባል ሰው ወይም ወሮበላ ሊሆን ይችላል” ብሏል። ነገር ግን ክርስቶስ እንዲህ ዓይነት ሰዎችን ይጠቀምባቸዋል ብለህ ታምናለህን?
ያም ሆነ ይህ ጵጵስናን ያቋቋመው ኢየሱስ ነው የሚለው አባባል በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ድጋፍ የለውም። የሃይማኖት ኢንሳይክሎፔዲያና ዘመናዊ የካቶሊክ ምሁራን ሳይቀሩ “ኢየሱስ በቤተክርስቲያን ውስጥ ጵጵስናን ቋሚ ሥልጣን አድርጎ ስለ መመሥረቱ ቀጥተኛ የመጽሐፍ ቅዱስ ማስረጃ የለም”በማለት ሳይሸሽጉ እውነቱን ተናግረዋል።