ሮማዊው ደግ የመቶ አለቃ
የሮማውያን የመቶ አለቃዎች በደግነታቸው ስማቸው የተጠራ አልነበሩም። የጦር ልምድ ያላቸውን መቶ ወታደሮች እንዲመራ የሚመደበው የመቶ አለቃ ቅጣት አስፈጻሚ፣ አንዳንዴም የሞት ፍርድ አስፈጻሚ ስለነበር ጨካኝና የማያወላውል ስነ ሥርዓት አስከባሪ መሆን ነበረበት። ይሁን እንጂ መጽሐፍ ቅዱስ የአውግስጦስ ጭፍራ መቶ አለቃ ስለሆነና ለሐዋርያው ጳውሎስ ደግሞ እውነተኛ ቸርነት ወይም ለጋስነትና ርኅራኄ ስላሳየ ሮማዊ ሰው ይነግረናል። የዚህ መቶ አለቃ ስም ማን ነበር? ዩልዮስ ይባል ነበር።
መጽሐፍ ቅዱስ ከዚህ ሰው ጋር የሚያስተዋውቀን በሐዋርያት ሥራ ምዕራፍ 27 ላይ ነው። ሐዋርያው ጳውሎስ ሮም ሄዶ ይግባኙን ለቄሣር ለማሰማት ጠይቆ ነበር። ስለዚህ ጳውሎስ ከሌሎች አያሌ እሥረኞች ጋር “ከአውግስጦስ ጭፍራ ለነበረ ዩልዮስ ለሚባል ለመቶ አለቃ” ጠባቂነት ተሰጠ። የመርከብ ጉዞአቸውን የጀመሩት ከኢየሩሳሌም በስተሰሜን ምዕራብ በምትገኘው ለሮማውያን ሠራዊት ደግሞ እንደ ጠቅላይ መምሪያ ታገለግል ከነበረችው ከቂሣሪያ የባሕር ወደብ ነው። ታሪክ ጸሐፊው ሉቃስ “በነገውም ወደ ሲዶና ስንደርስ ዩልዮስ ለጳውሎስ ቸርነት አድርጎ እርዳታቸውን ይቀበል ዘንድ ወደ ወዳጆቹ እንዲሄድ ፈቀደለት” ይላል።—ሥራ 27:1-3
ዩልዮስ ለጳውሎስ እንዲህ ዓይነት ቸርነት ለማድረግ ለምን እንደተነሣሣ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ አልተገለጸም። ለጳውሎስ የተለየ አያያዝ እንዲያደርግለት ከአገረ ገዥው ከፊስጦስ ልዩ ትዕዛዝ ተቀብሎ ሊሆን ይችላል ወይም ምናልባት ጳውሎስ የተያዘበትን ሁኔታ በማወቅ ድፍረቱንና ፍጹም አቋም ጠባቂነቱን ስላደነቀ ይሆናል። ያም ሆነ ይህ ዩልዮስ ጳውሎስ ተረ እስረኛ እንዳልሆነ የተገነዘበ ይመስላል።
ይሁን እንጂ ዩልዮስ መልካም ወደብ ከሚሏት ስፍራ ሲነሱ ጳውሎስ የሰጠውን ምክር ለመስማት አልመረጠም። ወዲያው መርከቧን በሰሜን አፍሪካ አካባቢ ከየብሱ አርቆ አሸዋ ላይ ሊተክላት በቃጣ ኃይለኛ ነፋስ ተያዘች። (ሥራ 27:8-17) በዚህ ኃይለኛ ንፋስ መሃል ጳውሎስ በድንጋጤ በተዋጡት መንገደኞች መሃል ቆመና “ከእናንተ አንድ ነፍስ እንኳ አይጠፋም” በማለት አረጋገጠላቸው። ያም ሆኖ አንዳንዶቹ መርከበኞች ከመርከቡ ለማምለጥ ሞከሩ። ይህን ጊዜ ጳውሎስ ለዩልዮስ “እነዚህ ሰዎች በመርከቡ ካልቆዩ እናንተ ትድኑ ዘንድ አትችሉም” ብሎ ነገረው።—ሥራ 27:21, 22, 30, 31
በዚህ ጊዜ ግን ዩልዮስ ጳውሎስን ለመስማት መረጠና መርከበኞቹ ሳይሸሹ ቀሩ። ጳውሎስ እንደተነበየው መርከቡ በባሕር ዳር በነበረ የአሸዋ ክምር ላይ ተተከለና ተሰበረ። ወታደሮቹ እስረኞቹ ያመልጣሉ ብለው በመፍራት ሁሉንም ሊገድሏቸው ወሰኑ። ዩልዮስ ግን አሁንም እንደገና በጉዳዩ ጣልቃ በመግባት የጳውሎስን ሕይወት አዳነው።—ሥራ 27:32, 41-44
ይህ ደግ የመቶ አለቃ በኋላ ምን እንደሆነ፣ የክርስትናን እምነት ይቀበል አይቀበል መጽሐፍ ቅዱስ አይናገርም። የደግነት ባሕርይ ማሳየቱ ግን ከአምላክ የተሰጠው ሕሊና ምን ዓይነት ውጤት ሊኖረው እንደሚችል ያመለክታል። (ሮሜ 2:14, 15) ይሁን እንጂ ክርስቲያኖች ሰብአዊ ቸርነት በማሳየት ብቻ ሳይወሰኑ ከአምላክ መንፈስ የሚገኘውን አምላካዊ ደግነት ያሳያሉ። (ገላትያ 5:22) በእርግጥ አንድ አምላክን ያላወቀ አረማዊ ወታደር ደግነት ማሳየት ከቻለ የአምላክ ሕዝቦች የበለጠ ደግነት ለማሳየት መነሣሣት ይገባቸዋል።