የጥያቄ ሣጥን
◼ አቅኚዎችን በየትኞቹ ተግባራዊ መንገዶች መርዳት እንችላለን?
በ2009 የአገልግሎት ዓመት በዓለም ዙሪያ 800,000 ገደማ የሚሆኑ ወንድሞችና እህቶች የዘወትር አቅኚዎች እና ልዩ አቅኚዎች በመሆን አገልግለዋል። እነዚህ የሙሉ ጊዜ አገልጋዮች የመንግሥቱን ምሥራች ለማስፋፋት ሲሉ ካላቸው ጊዜ፣ ጉልበትና ሀብት ውስጥ ‘በኩሩን’ ለይሖዋ መሥዋዕት አድርገው ሰጥተዋል። (ምሳሌ 3:9) ይሖዋ ባደረጉ ጥረት ምን ያህል ተደስቶ ይሆን! እኛስ የይሖዋን አመለካከት ማንጸባረቅ የምንችለው እንዴት ነው? አቅኚዎቻችን ደስታ እንዲያገኙ ብሎም በዚህ የአገልግሎት ዘርፍ እንዲጸኑ ምን አስተዋጽኦ ማድረግ እንችላለን?
ታስቦባቸው የተነገሩ ቃላት በአቅኚነት አገልግሎት እንዲቀጥሉ እንደሚያበረታታቸው ምንም ጥርጥር የለውም። (ምሳሌ 25:11) ከእነሱ ጋር በአገልግሎት ለመካፈል በሳምንታዊ ፕሮግራማችን ላይ ማስተካከያ ማድረግ እንችል ይሆን? አብረናቸው ስናገለግል በእነሱ መኪና ሳይሆን በእኛ መኪና ለመጠቀም ሐሳብ ልናቀርብላቸው ወይም የትራንስፖርት ልንከፍልላቸው እንችላለን። በእነሱ መኪና መጠቀም የሚኖርብን ከሆነ ደግሞ ለነዳጅ አስተዋጽኦ ልናደርግ እንችላለን። (1 ቆሮ. 13:5፤ ፊልጵ. 2:4) ከዚህም በተጨማሪ የእንግዳ ተቀባይነት መንፈስ በማሳየትና አልፎ አልፎ አብረውን ምግብ እንዲበሉ ቤታችን በመጋበዝ ፍቅራዊ ድጋፍ ልናደርግላቸው እንችላለን።—1 ጴጥ. 4:8, 9
ቅዱሳን መጻሕፍት፣ ይሖዋ መንግሥቱን ለሚያስቀድሙ ሰዎች የሚያስፈልጓቸውን ነገሮች እንደሚያሟላላቸው ዋስትና ይሰጣሉ። (መዝ. 37:25፤ ማቴ. 6:33) ይሖዋ ይህንን ለማድረግ ከሚጠቀምባቸው መንገዶች መካከል አፍቃሪ የሆኑት ክርስቲያን ወንድሞቻችን ይገኙበታል። (1 ዮሐ. 3:16-18) እርግጥ ነው አቅኚዎች ከገንዘብ ጋር በተያያዘ ያሉባቸውን ኃላፊነቶች ሌሎች እንዲሸከሙላቸው አይጠብቁም። እንዲሁም ችግር ሲያጋጥማቸው ሌሎች እንዲያውቁላቸው የተለየ ጥረት አያደርጉም። ይሁንና ንቁና አስተዋይ በመሆን የታማኝ አቅኚዎችን ‘ጉድለት በመሸፈን’ ተግባራዊ በሆኑ መንገዶች ልንረዳቸው እንችላለን።—2 ቆሮ. 8:14, 15
በመጀመሪያው መቶ ዘመን የክንክራኦስ ጉባኤ ቀናተኛ ወንጌላዊ የነበረችው ፌበን ወደ ሮም ስትጓዝ ጳውሎስ በሮም ለነበሩ ወንድሞች “ለቅዱሳን በሚገባ ሁኔታ በጌታ እንድትቀበሏትና ከእናንተ የምትፈልገውን ማንኛውንም ነገር በማድረግ እንድትረዷት” የሚል ማሳሰቢያ ሰጥቷቸው ነበር። (ሮም 16:1, 2) እኛም በጉባኤያችን ውስጥ ደከመኝ ሰለቸኝ ሳይሉ የመንግሥቱን ምሥራች ለሚሰብኩ የዘወትር አቅኚዎች እና ልዩ አቅኚዎች እንዲህ ዓይነቱን ፍቅራዊ ድጋፍ የምናሳይበት አጋጣሚ አለን።—ሥራ 5:42