የአንባቢያን ጥያቄዎች
የምሳሌ 30:18, 19 ጸሐፊ ‘ሰው ከሴት ልጅ ጋር የሚሄድበት መንገድ ከመረዳት አቅሙ በላይ’ እንደሆነ ተናግሯል። እንዲህ ሲል ምን ማለቱ ነበር?
እነዚህ ቃላት አንዳንድ ምሁራንን ጨምሮ ለብዙዎች እንቆቅልሽ ሆነው ኖረዋል። አዲስ ዓለም ትርጉም ላይ ሙሉው ጥቅስ እንዲህ ይላል፦ “ከመረዳት አቅሜ በላይ የሆኑ [ወይም “እጅግ የሚያስደንቁኝ” ግርጌ] ሦስት ነገሮች አሉ፤ የማልገነዘባቸውም አራት ነገሮች አሉ፦ ንስር በሰማያት የሚበርበት መንገድ፣ እባብ በዓለት ላይ የሚሄድበት መንገድ፣ መርከብ በባሕር ላይ የሚጓዝበት መንገድ፣ ሰውም ከሴት ልጅ ጋር የሚሄድበት መንገድ ናቸው።”—ምሳሌ 30:18, 19
ቀደም ሲል “[ሰው] ከሴት ልጅ ጋር የሚሄድበት መንገድ” የሚለውን አገላለጽ በአሉታዊ መንገድ እንረዳው ነበር። ለምን? ከላይ ያሉት ጥቅሶች “በቃኝ” ስለማያውቁ መጥፎ ነገሮች ይናገራሉ። (ምሳሌ 30:15, 16) ቁጥር 20 ደግሞ “ምንም የሠራሁት ጥፋት የለም” ስለምትል “አመንዝራ ሴት” ይናገራል። በመሆኑም ጥቅሱ በሰማያት ላይ እንደሚበር ንስር፣ በዓለት ላይ እንደሚሄድ እባብ ወይም በባሕር ላይ እንደሚጓዝ ጥንታዊ መርከብ ሰውየውም ማንም ሳያውቅበት የፈለገውን ነገር እንደሚያደርግ የሚያመለክት እንደሆነ እናስብ ነበር። ከዚህ አንጻር ‘ሰው ከሴት ልጅ ጋር የሚሄድበት መንገድ’ የሚለው አገላለጽ መጥፎ ነገርን ማለትም አንድ ተንኮለኛ ወጣት ተሞክሮ የሌላትን ልጅ በማማለል ሳታውቀው መጥፎ ነገር እንድትፈጽም እንደሚያደርጋት የሚያመለክት እንደሆነ ይሰማን ነበር።
ሆኖም ይህን ሐሳብ በአዎንታዊ መንገድ ለመረዳት የሚያበቃ ምክንያት አለ። ጸሐፊው፣ የጠቀሳቸው ነገሮች እንደሚያስደንቁት መግለጹ ብቻ ነበር።
የዕብራይስጡ በኩረ ጽሑፍ ይህ ጥቅስ አዎንታዊ ነገርን ሊያመለክት እንደሚችል ይጠቁማል። ቲኦሎጂካል ሌክሲከን ኦቭ ዚ ኦልድ ቴስታመንት የተባለው መጽሐፍ እንደገለጸው ምሳሌ 30:18 ላይ “ከመረዳት አቅሜ በላይ የሆኑ” ተብሎ የተተረጎመው የዕብራይስጥ ቃል “አስገራሚ፣ የማይቻል የሚመስል፣ አልፎ ተርፎም እጅግ አስደናቂ የሆነን ነገር ያመለክታል።”
በዩናይትድ ስቴትስ በሚገኘው ሃርቫርድ ዩኒቨርሲቲ የሚሠሩት ክሮፈርድ ቶይ የተባሉት ፕሮፌሰርም ይህ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅስ አሉታዊ ነገርን የሚያመለክት እንዳልሆነ ገልጸዋል። እንዲህ ብለዋል፦ “ጸሐፊው የተዘረዘሩት ነገሮች አስደናቂ መሆናቸውን መግለጹ ነበር።”
በመሆኑም ምሳሌ 30:18, 19 እጅግ አስደናቂ አልፎ ተርፎም ከመረዳት አቅማችን በላይ የሆኑ ነገሮችን የሚገልጽ ነው ብሎ መደምደሙ ምክንያታዊ ይመስላል። እንደ ምሳሌ መጽሐፍ ጸሐፊ ሁሉ እኛም ንስር በሰማያት ላይ የሚበርበት መንገድ፣ እግር የሌለው እባብ በዓለት ላይ የሚሄድበት መንገድ፣ ግዙፍ መርከብ በባሕር ላይ የሚጓዝበት መንገድ እንዲሁም አንድ ወጣት ወንድና አንዲት ወጣት ሴት ተዋደው በደስታ አብረው የሚኖሩበት መንገድ በጣም ያስገርመናል።