-
ከሚያምኑት ወገን እንሁንመጠበቂያ ግንብ—1999 | ታኅሣሥ 15
-
-
በአምላክ ቃል በጥሩ ሁኔታ መጠቀም
6. ጳውሎስ በዕብራውያን 10:38 ላይ ተመዝግበው የሚገኙትን ቃላት የጠቀሰው ከየት ነው?
6 በተጨማሪም ጳውሎስ ቅዱሳን ጽሑፎችን በጥበብ በመጠቀም የእምነት አጋሮቹን እምነት ገንብቷል። ለምሳሌ ያህል “ጻድቅ ግን በእምነት ይኖራል ወደ ኋላም ቢያፈገፍግ፣ ነፍሴ በእርሱ ደስ አይላትም” ሲል ጽፏል። (ዕብራውያን 10:38) እዚህ ላይ ጳውሎስ ነቢዩ ዕንባቆም የተናገረውን መጥቀሱ ነበር።a እነዚህ ቃላት የትንቢት መጻሕፍትን ጠንቅቀው ለሚያውቁት የጳውሎስ አንባቢዎች ማለትም ለዕብራውያን ክርስቲያኖች እንግዳ እንዳልሆኑ ግልጽ ነው። በ61 እዘአ በኢየሩሳሌምና በአቅራቢያዋ የሚገኙ ክርስቲያኖችን እምነት ለማጠንከር ከነበረው ግብ አንጻር ጳውሎስ የዕንባቆምን ምሳሌ ለመጠቀም መምረጡ የተገባ ነበር። ለምን?
7. ዕንባቆም ትንቢቱን የመዘገበው መቼ ነው? በዚያን ወቅት በይሁዳ የነበረው ሁኔታ ምን ይመስል ነበር?
7 ከሁኔታዎች ለመረዳት እንደሚቻለው ዕንባቆም መጽሐፉን የጻፈው ኢየሩሳሌም በ607 ከዘአበ ከመጥፋቷ ከሁለት አሥርተ ዓመታት በፊት ነበር። ‘መራርና ፈጣን’ ሕዝብ የሆኑት ከለዳውያን (ወይም ባቢሎናውያን) ድንገት በይሁዳ ላይ እንደሚነሱና ኢየሩሳሌምን እንደሚያጠፉ እንዲሁም ሕዝቡንም ሆነ ነገሥታቶቻቸውን እንደሚውጡ ነቢዩ በራእይ ተመልክቶ ነበር። (ዕንባቆም 1:5-11) ሆኖም እንዲህ ዓይነት ጥፋት እንደሚመጣ ትንቢት የተነገረው ከአንድ መቶ ዓመት ከሚበልጥ ጊዜ በፊት ማለትም ከኢሳይያስ ዘመን ጀምሮ ነበር። በዕንባቆም ዘመን ጥሩ ንጉሥ በነበረው በኢዮስያስ ምትክ ኢዮአቄም ነግሦ የነበረ ሲሆን ይህም በይሁዳ ክፋት እንደገና እንዲስፋፋ አደረገ። ኢዮአቄም በይሖዋ ስም የሚናገሩ ሰዎችን ያሳድድ አልፎ ተርፎም ይገድል ነበር። (2 ዜና መዋዕል 36:5፤ ኤርምያስ 22:17፤ 26:20-24) በጭንቀት የተዋጠው ነቢዩ ዕንባቆም “አቤቱ፣ እኔ ስጮኽ የማትሰማው እስከ መቼ ነው?” በማለት ሮሮ ማሰማቱ አያስገርምም።—ዕንባቆም 1:2
8. የዕንባቆም ምሳሌ በመጀመሪያው መቶ ዘመን ለነበሩትም ሆነ ዛሬ ላሉት ክርስቲያኖች ጠቃሚ የሆነው ለምንድን ነው?
8 ዕንባቆም የኢየሩሳሌም ጥፋት ምን ያህል እንደቀረበ አያውቅም ነበር። በተመሳሳይም የመጀመሪያው መቶ ዘመን ክርስቲያኖች የአይሁድ የነገሮች ሥርዓት ፍጻሜ መቼ እንደሚሆን አያውቁም ነበር። እኛም ብንሆን በዚህ ክፉ የነገሮች ሥርዓት ላይ የይሖዋ ፍርድ የሚጀምርበትን ‘ቀንና ሰዓት’ አናውቅም። (ማቴዎስ 24:36) እንግዲያው ይሖዋ ለዕንባቆም የሰጠውን ድርብ መልስ ልብ እንበል። በመጀመሪያ ደረጃ ፍጻሜው ከተቀጠረለት ጊዜ ዝንፍ እንደማይል ለነቢዩ አረጋገጠለት። በሰብዓዊ አመለካከት የዘገየ ቢመስልም እንኳ አምላክ “አይዘገይም” ሲል ተናግሯል። (ዕንባቆም 2:3) በሁለተኛ ደረጃ ደግሞ ይሖዋ “ጻድቅ በእምነቱ በሕይወት ይኖራል” በማለት ለዕንባቆም ነገረው። (ዕንባቆም 2:4) ይህ እንዴት ያለ ግሩምና ለመረዳት የማይከብድ እውነት ነው! ትልቅ ለውጥ የሚያመጣው መጨረሻው የሚመጣበት ጊዜ ሳይሆን የእኛ በእምነት መቀጠል አለመቀጠል ነው።
9. ታዛዥ የሆኑ የይሖዋ አገልጋዮች ታማኝ ሆነው በመገኘታቸው (ሀ) በ607 ከዘአበ (ለ) ከ66 እዘአ በኋላ በሕይወት ሊተርፉ የቻሉት እንዴት ነው? (ሐ) እምነታችንን ማጎልበታችን በጣም አስፈላጊ የሆነው ለምንድን ነው?
9 ኢየሩሳሌም በ607 ከዘአበ በጠፋችበት ወቅት ኤርምያስ፣ የእሱ ጸሐፊ የነበረው ባሮክ፣ አቤሜሌክና ታማኞቹ ሬካባውያን ይሖዋ ለዕንባቆም የሰጠው ተስፋ ሲፈጸም ተመልክተዋል። በኢየሩሳሌም ላይ ከደረሰው አሰቃቂ ጥፋት ተርፈው ‘በሕይወት መኖራቸውን ቀጥለዋል።’ ለምን? ይሖዋ ለታማኝነታቸው ወሮታ ስለከፈላቸው ነው። (ኤርምያስ 35:1-19፤ 39:15-18፤ 43:4-7፤ 45:1-5) በተመሳሳይም በመጀመሪያው መቶ ዘመን የነበሩት ዕብራውያን ክርስቲያኖች ለጳውሎስ ምክር አዎንታዊ ምላሽ ሰጥተው መሆን አለበት። ምክንያቱም በ66 እዘአ የሮማ ሠራዊት በኢየሩሳሌም ላይ ጥቃት መሰንዘር ከጀመረ በኋላ ባልታወቀ ምክንያት ወደ ኋላ ሲያፈገፍግ በወቅቱ የነበሩት ክርስቲያኖች ኢየሱስ ወደ ተራራ ስለመሸሽ የሰጠውን ማስጠንቀቂያ በታማኝነት ተግባራዊ አድርገዋል። (ሉቃስ 21:20, 21) በሕይወት መኖራቸውን መቀጠል የቻሉት ታማኝ ሆነው በመገኘታቸው ነው። እኛም በተመሳሳይ መጨረሻው በሚመጣበት ጊዜ ታማኝ ሆነን ከተገኘን በሕይወት መኖራችንን እንቀጥላለን። ከአሁኑ እምነታችንን እንድናጠነክር የሚያበረታታ እንዴት ያለ ግሩም ሐሳብ ነው!
-
-
ከሚያምኑት ወገን እንሁንመጠበቂያ ግንብ—1999 | ታኅሣሥ 15
-
-
a ጳውሎስ የጠቀሰው በሰፕቱጀንት መሠረት “ማንም ወደ ኋላ ቢያፈገፍግ ነፍሴ በእሱ ደስ አይላትም” የሚል ሐረግ የሚጨምረውን ዕንባቆም 2:4ን ነበር። ይህ አገላለጽ አሁን በእጅ ባሉ የብራና ዕብራይስጥ ጽሑፎች ውስጥ በአንዳቸውም ላይ አይገኝም። አንዳንዶች ሰፕቱጀንት የተገለበጠው አሁን በእጅ በማይገኙ በጣም ጥንታዊ የብራና ጽሑፎች ላይ ነው የሚል አስተያየት ይሰጣሉ። ያም ሆነ ይህ ጳውሎስ በመንፈስ ቅዱስ አነሳሽነት ይህን ጥቅስ በመልእክቱ ውስጥ ጨምሮታል። ስለዚህ ይህ ሐሳብ መለኮታዊ ድጋፍ አለው ማለት ነው።
-