-
ይሖዋ ምክንያታዊ ነው!መጠበቂያ ግንብ—1994 | ነሐሴ 1
-
-
ምክንያታዊነት የመለኮታዊ ጥበብ መለያ ባሕርይ ነው
6. ያዕቆብ መለኮታዊ ጥበብን ሲገልጽ የተጠቀመበት የግሪክኛ ቃል ቀጥተኛ ትርጉሙና ቃሉ የሚያመለክታቸው ነገሮች ምንድን ናቸው?
6 ራሱን ከማንም በላይ ከሁኔታዎች ጋር ማስማማት የሚችለው አምላክ ያለውን ጥበብ ለመግለጽ ደቀ መዝሙሩ ያዕቆብ አንድ ጥሩ ቃል ተጠቅሟል። “ላይኛይቱ ጥበብ . . . ምክንያታዊ ናት” ሲል ጽፏል። (ያዕቆብ 3:17 አዓት) እዚህ ላይ የገባው የግሪክኛ ቃል (ኤፒኤኬስ) ለትርጉም አስቸጋሪ ነው። ተርጓሚዎች “ገር፣” “ላላ ያለ፣” “ቻይ” እና “አሳቢ” የሚሉትን የመሰሉ ቃላት ተጠቅመዋል። የአዲሲቱ ዓለም ትርጉም በግርጌ ማስታወሻው ላይ ቃሉ በቀጥታ ሲተረጎም “እሺ ባይ” ማለት መሆኑን በማመልከት “ምክንያታዊ” በማለት ተርጉሞታል።a በተጨማሪም ቃሉ የሕጉ ፊደል ካልተፈጸመ ብሎ አለማክረርን፣ ከመጠን በላይ ጥብቅ ወይም የማያወላዳ አለመሆንን ያመለክታል። የመጽሐፍ ቅዱስ ምሁር የሆኑት ዊልያም ባርክሌይ በኒው ቴስታመንት ወርድስ ላይ የሚከተለውን ሐሳብ ሰጥተዋል፦ “ኤፒኤኪያን በተመለከተ ዋናውና መሠረታዊው ነገር ከአምላክ የመነጨ መሆኑ ነው። አምላክ መብቱን ቀጥ አድርጎ ቢያስጠብቅ ኖሮና ውልፍት የማያደርጉ የሕጉን የአቋም ደረጃዎች በእኛ ላይ ቢያውላቸው ኖሮ ምን እንሆን ነበር? አምላክ ኤፒኤኪስ በመሆንና ሌሎችን በኤፒኤኪያ በመያዝ ረገድ ወደር የለውም።”
7. ይሖዋ በኤደን ገነት ውስጥ ምክንያታዊነትን ያሳየው እንዴት ነው?
7 የሰው ልጅ በይሖዋ ሉዓላዊነት ላይ ያመፀበትን ጊዜ ወደ ኋላ መለስ ብለህ ተመልከት። ሦስቱን ውለታ ቢስ ዓመፀኞች አዳምን፣ ሔዋንና ሰይጣንን የእጃቸውን እንዲያገኙ በሞት መቅጣት ለአምላክ ምንኛ ቀላል ነበር! እንዲህ በማድረግም ከሚደርስበት ሐዘን ምንኛ በተገላገለ ነበር! እንዲህ ያለ የማያወለዳ የፍትሕ እርምጃ የመውሰድ መብት የለውም ብሎ መከራከር የሚችል ማነው? ሆኖም ይሖዋ ሰማያዊ ሰረገላ መሰል ድርጅቱን ድርቅ ባለና ራሱን ከሁኔታዎች ጋር በማያስማማ የፍትሕ ደንብ መርቶት አያውቅም። ስለዚህ ይህ ሰረገላ ግትር አቋም ይዞ በመጓዝ ሰብዓዊውን ቤተሰብና የሰውን ዘር የወደፊት አስደሳች ተስፋዎች አልደመሰሰም። በተቃራኒው ይሖዋ ሰረገላውን በመብረቅ ፍጥነት አቅጣጫውን እንዲቀይር አድርጎቷል። ዓመፁ እንደተፈጸመ ወዲያውኑ ይሖዋ አምላክ ለአዳም ዘሮች በሙሉ ምሕረትና ተስፋን የዘረጋ የረጅም ጊዜ ዓላማ አወጣ።—ዘፍጥረት 3:15
8. (ሀ) ሕዝበ ክርስትና ለምክንያታዊነት ያላት የተሳሳተ አመለካከት ይሖዋ ካለው እውነተኛ ምክንያታዊነት ጋር ሊነጻጸር የሚችለው እንዴት ነው? (ለ) ይሖዋ ያለው ምክንያታዊነት መለኮታዊ የሆኑ መሠረታዊ ሥርዓቶቹን እንዲጥስ አያደርገውም ለማለት የምንችለው ለምንድን ነው?
8 ይሖዋ ምክንያታዊ ነው ማለት ግን መለኮታዊ የሆኑ መሠረታዊ ሥርዓቶቹን ይጥሳል ማለት አይደለም። በዛሬው ጊዜ የሕዝበ ክርስትና ቤተ ክርስቲያኖች ያሻቸውን በሚያደርጉት ሙልጭልጭ በሚሉ መንጎቻቸው ዘንድ ተቀባይነትን ለማግኘት የጾታ ብልግናን በቸልታ ሲያልፉ ምክንያታዊ የሆኑ መስሎ ሊታያቸው ይችላል። (ከ2 ጢሞቴዎስ 4:3 ጋር አወዳድር።) ይሖዋ ሕግጋቱን አያፈርስም፤ ወይም መሠረታዊ ሥርዓቶቹን አይጥስም። ከዚህ ይልቅ ግትር ላለመሆን ማለትም ከሁኔታዎች ጋር ራሱን ለማስማማት ፈቃደኝነቱን አሳይቷል። በዚህ መንገድ መሠረታዊ ሥርዓቶቹ በትክክልና በይቅር ባይነት መንፈስ በሥራ ሊውሉ ይችላሉ። ፍትሑንና ኃይሉን ከፍቅሩና ከምክንያታዊ ጥበቡ ጋር በተመጣጠነ ሁኔታ በሥራ የሚያውልበትን መንገድ ጠንቅቆ ያውቃል። ይሖዋ ምክንያታዊነትን በሥራ ያሳየባቸውን ሦስት መንገዶች እስቲ እንመልከት።
“ይቅር ለማለት ዝግጁ ነህ”
9, 10. (ሀ) ‘ይቅር ለማለት ዝግጁ መሆን’ ከምክንያታዊነት ጋር ምን ዝምድና አለው? (ለ) ዳዊት ይሖዋ ይቅር ለማለት ዝግጁ በመሆኑ የተጠቀመው እንዴት ነው? ለምንስ?
9 ዳዊት “አቤቱ፣ አንተ ጥሩና ይቅር ለማለት ዝግጁ ነህ፤ ፍቅራዊ ደግነትህም ለሚጠሩህ ሁሉ ብዙ ነውና” ሲል ጽፏል። (መዝሙር 86:5 አዓት) የዕብራይስጥ ቅዱሳን ጽሑፎች ወደ ግሪክኛ ሲተረጎሙ “ይቅር ለማለት ዝግጁ ነህ” የሚለው ሐረግ ኤፒኤኬስ ወይም “ምክንያታዊ” ተብሎ ተተርጉሟል። በእርግጥም ምክንያታዊነትን ለማንጸባረቅ ቁልፉ ይቅር ለማለት ዝግጁ መሆንና ምሕረትን ማሳየት ሳይሆን አይቀርም።
10 ዳዊት ራሱ ይሖዋ በዚህ ረገድ ምን ያህል ምክንያታዊ እንደሆነ አሳምሮ ያውቅ ነበር። ዳዊት ከቤርሳቤህ ጋር ምንዝር በፈጸመበትና ባልዋን ለማስገደል ሁኔታዎችን ባመቻቸበት ጊዜ እሱም ሆነ ቤርሳቤህ የሞት ቅጣት ይገባቸው ነበር። (ዘዳግም 22:22፤ 2 ሳሙኤል 11:2–27) ጉዳዩን በፍርድ የተመለከቱት ግትር ሰብዓዊ ዳኞች ቢሆኑ ኖሮ ሁለቱም ሕይወታቸውን ሊያጡ ይችሉ ነበር። ይሖዋ ግን ምክንያታዊነትን (ኤፒኤኬስ) አሳይቷል። ይህንንም ቫይን ኤክስፖዚተሪ ዲክሽነሪ ኦቭ ቢብሊካል ዎርድስ “‘የአንድን ጉዳይ እውነታዎች በሰብአዊነትና በምክንያታዊነት’ የሚመለከትን አሳቢነት የሚገልጽ” ነው በማለት አስቀምጦታል። ይሖዋን ምሕረት እንዲያደርግ የገፋፉት እውነታዎች የኃጢአተኞቹ ልባዊ ጸጸትና ዳዊት ራሱ ቀደም ሲል ለሌሎች ያደረገው ምሕረት ጭምር ሊሆኑ ይችላሉ። (1 ሳሙኤል 24:4–6፤ 25:32–35፤ 26:7–11፤ ማቴዎስ 5:7፤ ያዕቆብ 2:13) ሆኖም ይሖዋ በዘጸአት 34:4–7 ላይ ስለ ራሱ ከሰጠው መግለጫ ጋር በሚስማማ መንገድ ለዳዊት እርማት መስጠቱ ምክንያታዊ ነበር። ዳዊት የይሖዋን ቃል ማቃለሉን እንዲገነዘብ የሚያደርግ ኃይለኛ መልዕክት አስይዞ ነቢዩ ናታንን ወደ ዳዊት ላከው። ዳዊት በመጸጸቱ በሠራው ኃጢአት አልሞተም።—2 ሳሙኤል 12:1–14
-
-
ይሖዋ ምክንያታዊ ነው!መጠበቂያ ግንብ—1994 | ነሐሴ 1
-
-
a በ1769 የመዝገበ ቃላት አዘጋጅ የሆኑት ጆን ፓርክኸርስት ቃሉን “እሺ ባይ፣ ረጋ ያለ፣ ገር፣ ታጋሽ” ብለው ተርጉመውታል። ሌሎች የመጽሐፍ ቅዱስ ምሁራንም “እሺ ባይ” ብለው ተርጉመውታል።
-