6 ሊጠቅመን ይችላል?
ጸሎት የሚያስገኝልን ጥቅም አለ? አዎን፣ መጽሐፍ ቅዱስ ታማኝ የአምላክ አገልጋዮች መጸለያቸው በእርግጥ እንደሚጠቅማቸው ይናገራል። (ሉቃስ 22:40፤ ያዕቆብ 5:13) እንዲያውም መጸለይ መንፈሳዊና ስሜታዊ አልፎ ተርፎም አካላዊ ጥቅም ያስገኝልናል። እንዴት?
ስጦታ የተሰጠው አንድ ልጅ አለህ እንበል። ‘የአመስጋኝነት ስሜት ከተሰማህ ግድ የለም ይበቃል’ ትለዋለህ? ወይስ ምስጋናውን እንዲገልጽ ታስተምረዋለህ? በጎ የሆኑ ስሜቶቻችንን አውጥተን በቃላት ስንገልጽ ስለዚያ ስሜት በደንብ የምናስብ ከመሆኑም በላይ ይበልጥ እናዳብረዋለን። ስሜታችንን ለአምላክ በምንገልጽበት ጊዜስ ሁኔታው ተመሳሳይ ነው? ምንም ጥያቄ የለውም! አንዳንድ ምሳሌዎችን እንመልከት።
የምስጋና ጸሎት። ላገኘናቸው መልካም ነገሮች ሁሉ አባታችንን ስናመሰግነው ባገኘናቸው በረከቶች ላይ እናተኩራለን። በዚህም ምክንያት ይበልጥ አመስጋኝ፣ ደስተኛና አዎንታዊ አመለካከት ያለን ሰዎች እንሆናለን።—ፊልጵስዩስ 4:6
ምሳሌ፦ ኢየሱስ፣ ያቀረባቸውን ጸሎቶች ሰምቶ ምላሽ ስለሰጠው አባቱን አመስግኖታል።—ዮሐንስ 11:41
ይቅርታ ለማግኘት የሚቀርብ ጸሎት። አምላክን ይቅርታ ስንጠይቀው ሕሊናችንን ይበልጥ እናሠለጥነዋለን፣ ልባዊ ንስሐ እንገባለን እንዲሁም ኃጢአት ያለውን ክብደት የበለጠ እንገነዘባለን። በተጨማሪም የጥፋተኝነት ስሜት ከሚፈጥረው ጭንቀት እፎይታ እናገኛለን።
ምሳሌ፦ ዳዊት ንስሐ መግባቱን ለማሳየትና ሐዘኑን ለመግለጽ ጸልዮ ነበር።—መዝሙር 51
መመሪያና ጥበብ ለማግኘት የሚቀርብ ጸሎት። ይሖዋን እንዲመራንና ጥሩ ውሳኔ እንድናደርግ የሚያስፈልገንን ጥበብ እንዲሰጠን መለመናችን፣ ይበልጥ ትሑቶች እንድንሆን ሊረዳን ይችላል። በተጨማሪም ያለብንን የአቅም ገደብ የሚያስታውሰን ከመሆኑም ሌላ በሰማይ በሚኖረው አባታችን ላይ እምነት እንድንጥል ይረዳናል።—ምሳሌ 3:5, 6
ምሳሌ፦ ሰለሞን የእስራኤልን ሕዝብ ለማስተዳደር የሚያስችለውን መመሪያና ጥበብ ለማግኘት አምላክን በትሕትና ጠይቋል።—1 ነገሥት 3:5-12
በጭንቀት ጊዜ የሚቀርብ ጸሎት። ስሜታችን እንዲረበሽ የሚያደርግ ሁኔታ ሲያጋጥመን ለአምላክ የሚሰማንን ሁሉ ብንነግረው ልባችን የሚረጋጋ ከመሆኑም በላይ በራሳችን ሳይሆን በይሖዋ እንታመናለን።—መዝሙር 62:8
ምሳሌ፦ ንጉሥ አሳ አደገኛ ጠላት በመጣበት ጊዜ ጸልዮ ነበር።—2 ዜና መዋዕል 14:11
ለሌሎች የሚቀርብ ጸሎት። እንዲህ ዓይነቱ ጸሎት የራስ ወዳድነትን ስሜት እንድናስወግድ አልፎ ተርፎም ይበልጥ ርኅሩኆችና የሌላው ሰው ችግር የሚገባን እንድንሆን ይረዳናል።
ምሳሌ፦ ኢየሱስ ለተከታዮቹ ጸልዮላቸዋል።—ዮሐንስ 17:9-17
የውዳሴ ጸሎት። ይሖዋን ላከናወናቸው አስደናቂ ሥራዎችና ለግሩም ባሕርያቱ ስናወድሰው ለእሱ ያለን አክብሮትና አድናቆት ይጨምራል። በተጨማሪም እንዲህ ያለው ጸሎት ወደ አምላካችንና ወደ አባታችን ይበልጥ እንድንቀርብ ይረዳናል።
ምሳሌ፦ ዳዊት አስደናቂ ፍጥረታትን በመጥቀስ አምላክን ከልብ በመነጨ ስሜት አወድሶታል።—መዝሙር 8
ጸሎት ሌላም በረከት ይኸውም ‘ከማሰብ ችሎታ ሁሉ በላይ የሆነውን የአምላክ ሰላም’ እንድናገኝ ይረዳናል። (ፊልጵስዩስ 4:7) በዚህ በመከራ በተሞላ ዓለም ውስጥ መረጋጋት መቻላችን በእርግጥም የማይገኝ በረከት ነው። እንዲህ ያለው የመረጋጋት ስሜት አካላዊ ጥቅምም ያስገኛል። (ምሳሌ 14:30) ይሁንና መረጋጋት በራሳችን ጥረት ብቻ የሚገኝ ነገር ነው? ወይስ ከእኛ ጥረት የበለጠ የሚያስፈልገን ሌላ ነገር አለ?
ጸሎት አካላዊና ስሜታዊ ከሁሉም በላይ ደግሞ መንፈሳዊ ጥቅም ያስገኝልናል