ሰኞ፣ መስከረም 15
ወንድሞች፣ በይሖዋ ስም የተናገሩትን ነቢያት መከራ በመቀበልና ትዕግሥት በማሳየት ረገድ አርዓያ አድርጋችሁ ተመልከቷቸው።—ያዕ. 5:10
መጽሐፍ ቅዱስ ትዕግሥት ያሳዩ በርካታ ሰዎችን ምሳሌ ይዟል። በግል ጥናትህ ላይ የእነዚህን ሰዎች ምሳሌ ለመመርመር ለምን አትሞክርም? ለአብነት ያህል፣ ዳዊት የእስራኤል ንጉሥ እንዲሆን የተቀባው ገና በልጅነቱ ቢሆንም ንግሥናውን እስኪቀበል ድረስ ለበርካታ ዓመታት መጠበቅ አስፈልጎታል። ስምዖን እና ሐና፣ ተስፋ የተሰጠበት መሲሕ እስኪመጣ በሚጠባበቁበት ወቅት ይሖዋን በታማኝነት ያገለግሉ ነበር። (ሉቃስ 2:25, 36-38) እንዲህ ያሉትን ዘገባዎች በምታጠናበት ወቅት የእነዚህን ጥያቄዎች መልስ ለመፈለግ ጥረት አድርግ፦ ይህ ሰው ትዕግሥት እንዲያሳይ የረዳው ምን ሊሆን ይችላል? ትዕግሥተኛ መሆኑ የጠቀመው እንዴት ነው? የእሱን ምሳሌ መከተል የምችለው እንዴት ነው? ትዕግሥት ስላላሳዩ ሰዎች ማጥናትህም ሊጠቅምህ ይችላል። (1 ሳሙ. 13:8-14) የሚከተሉትን ጥያቄዎች ልታነሳ ትችላለህ፦ ‘ትዕግሥት እንዳያሳይ ያደረገው ምን ሊሆን ይችላል? ትዕግሥት አለማሳየቱ ምን መዘዝ አስከትሎበታል?’ w23.08 25 አን. 15
ማክሰኞ፣ መስከረም 16
አንተ የአምላክ ቅዱስ አገልጋይ እንደሆንክ አምነናል፤ ደግሞም አውቀናል።—ዮሐ. 6:69
ሐዋርያው ጴጥሮስ ታማኝ ነበር፤ ምንም ነገር ኢየሱስን መከተሉን እንዲያስቆመው አልፈቀደም። በአንድ ወቅት ኢየሱስ የተናገረውን ነገር ደቀ መዛሙርቱ መረዳት ባቃታቸው ጊዜ ጴጥሮስ ታማኝ መሆኑን አሳይቷል። (ዮሐ. 6:68) ብዙዎች፣ ኢየሱስ ማብራሪያ እንዲሰጣቸው ሳይጠብቁ እሱን መከተላቸውን አቆሙ። ጴጥሮስ ግን እንደዚያ አላደረገም። “የዘላለም ሕይወት ቃል” ያለው ኢየሱስ ብቻ እንደሆነ ተገንዝቦ ነበር። ኢየሱስ ጴጥሮስና ሌሎቹ ሐዋርያት ትተውት እንደሚሄዱ አውቆ ነበር። ያም ቢሆን ኢየሱስ፣ ጴጥሮስ እንደሚመለስና ታማኝ ሆኖ እንደሚቀጥል እርግጠኛ ነበር። (ሉቃስ 22:31, 32) ኢየሱስ “መንፈስ ዝግጁ . . . ሥጋ ግን ደካማ” እንደሆነ ያውቅ ነበር። (ማር. 14:38) በመሆኑም ጴጥሮስ ከካደው በኋላም እንኳ ኢየሱስ ተስፋ አልቆረጠበትም። ኢየሱስ ከሞት ከተነሳ በኋላ ለጴጥሮስ ተገለጠለት፤ በዚህ ወቅት ጴጥሮስ ብቻውን ሳይሆን አይቀርም። (ማር. 16:7፤ ሉቃስ 24:34፤ 1 ቆሮ. 15:5) ቅስሙ የተሰበረው ይህ ሐዋርያ በዚህ ምንኛ ተጽናንቶ ይሆን! w23.09 22 አን. 9-10
ረቡዕ፣ መስከረም 17
የዓመፅ ሥራቸው ይቅር የተባለላቸው፣ ኃጢአታቸውም የተሸፈነላቸው ደስተኞች ናቸው።—ሮም 4:7
አምላክ በእሱ የሚያምኑ ሰዎችን ኃጢአታቸውን ይሰርዝላቸዋል ወይም ይሸፍንላቸዋል። ሙሉ በሙሉ ይቅር ይላቸዋል፤ እንዲሁም ኃጢአታቸውን አይቆጥርባቸውም። (መዝ. 32:1, 2) እንዲህ ያሉትን ሰዎች፣ እምነታቸውን መሠረት በማድረግ ነቀፋ የሌለባቸው ወይም ጻድቃን አድርጎ ይቆጥራቸዋል። አብርሃም፣ ዳዊትና ሌሎች ታማኝ የአምላክ አገልጋዮች ጻድቃን ተደርገው ቢቆጠሩም ፍጽምና የጎደላቸው ኃጢአተኞች ነበሩ። ሆኖም በእምነታቸው ምክንያት አምላክ ነቀፋ የሌለባቸው አድርጎ ቆጥሯቸዋል። በተለይ በእሱ ላይ እምነት ከሌላቸው ሰዎች ጋር ሲወዳደሩ ጻድቃን ተደርገው መቆጠራቸው ተገቢ ነው። (ኤፌ. 2:12) ሐዋርያው ጳውሎስ በደብዳቤው ላይ በግልጽ እንደተናገረው ከአምላክ ጋር የቅርብ ወዳጅነት ለመመሥረት እምነት የግድ አስፈላጊ ነው። አብርሃምና ዳዊት የአምላክ ወዳጅ መሆን የቻሉት እምነት ስለነበራቸው ነው። እኛም ብንሆን የአምላክ ወዳጅ ለመሆን እምነት ያስፈልገናል። w23.12 3 አን. 6-7