ማክሰኞ፣ መስከረም 16
አንተ የአምላክ ቅዱስ አገልጋይ እንደሆንክ አምነናል፤ ደግሞም አውቀናል።—ዮሐ. 6:69
ሐዋርያው ጴጥሮስ ታማኝ ነበር፤ ምንም ነገር ኢየሱስን መከተሉን እንዲያስቆመው አልፈቀደም። በአንድ ወቅት ኢየሱስ የተናገረውን ነገር ደቀ መዛሙርቱ መረዳት ባቃታቸው ጊዜ ጴጥሮስ ታማኝ መሆኑን አሳይቷል። (ዮሐ. 6:68) ብዙዎች፣ ኢየሱስ ማብራሪያ እንዲሰጣቸው ሳይጠብቁ እሱን መከተላቸውን አቆሙ። ጴጥሮስ ግን እንደዚያ አላደረገም። “የዘላለም ሕይወት ቃል” ያለው ኢየሱስ ብቻ እንደሆነ ተገንዝቦ ነበር። ኢየሱስ ጴጥሮስና ሌሎቹ ሐዋርያት ትተውት እንደሚሄዱ አውቆ ነበር። ያም ቢሆን ኢየሱስ፣ ጴጥሮስ እንደሚመለስና ታማኝ ሆኖ እንደሚቀጥል እርግጠኛ ነበር። (ሉቃስ 22:31, 32) ኢየሱስ “መንፈስ ዝግጁ . . . ሥጋ ግን ደካማ” እንደሆነ ያውቅ ነበር። (ማር. 14:38) በመሆኑም ጴጥሮስ ከካደው በኋላም እንኳ ኢየሱስ ተስፋ አልቆረጠበትም። ኢየሱስ ከሞት ከተነሳ በኋላ ለጴጥሮስ ተገለጠለት፤ በዚህ ወቅት ጴጥሮስ ብቻውን ሳይሆን አይቀርም። (ማር. 16:7፤ ሉቃስ 24:34፤ 1 ቆሮ. 15:5) ቅስሙ የተሰበረው ይህ ሐዋርያ በዚህ ምንኛ ተጽናንቶ ይሆን! w23.09 22 አን. 9-10
ረቡዕ፣ መስከረም 17
የዓመፅ ሥራቸው ይቅር የተባለላቸው፣ ኃጢአታቸውም የተሸፈነላቸው ደስተኞች ናቸው።—ሮም 4:7
አምላክ በእሱ የሚያምኑ ሰዎችን ኃጢአታቸውን ይሰርዝላቸዋል ወይም ይሸፍንላቸዋል። ሙሉ በሙሉ ይቅር ይላቸዋል፤ እንዲሁም ኃጢአታቸውን አይቆጥርባቸውም። (መዝ. 32:1, 2) እንዲህ ያሉትን ሰዎች፣ እምነታቸውን መሠረት በማድረግ ነቀፋ የሌለባቸው ወይም ጻድቃን አድርጎ ይቆጥራቸዋል። አብርሃም፣ ዳዊትና ሌሎች ታማኝ የአምላክ አገልጋዮች ጻድቃን ተደርገው ቢቆጠሩም ፍጽምና የጎደላቸው ኃጢአተኞች ነበሩ። ሆኖም በእምነታቸው ምክንያት አምላክ ነቀፋ የሌለባቸው አድርጎ ቆጥሯቸዋል። በተለይ በእሱ ላይ እምነት ከሌላቸው ሰዎች ጋር ሲወዳደሩ ጻድቃን ተደርገው መቆጠራቸው ተገቢ ነው። (ኤፌ. 2:12) ሐዋርያው ጳውሎስ በደብዳቤው ላይ በግልጽ እንደተናገረው ከአምላክ ጋር የቅርብ ወዳጅነት ለመመሥረት እምነት የግድ አስፈላጊ ነው። አብርሃምና ዳዊት የአምላክ ወዳጅ መሆን የቻሉት እምነት ስለነበራቸው ነው። እኛም ብንሆን የአምላክ ወዳጅ ለመሆን እምነት ያስፈልገናል። w23.12 3 አን. 6-7
ሐሙስ፣ መስከረም 18
የውዳሴ መሥዋዕት ዘወትር ለአምላክ እናቅርብ፤ ይህም ስሙን በይፋ የምናውጅበት የከንፈራችን ፍሬ ነው።—ዕብ. 13:15
በዛሬው ጊዜ ሁሉም ክርስቲያኖች ጊዜያቸውን፣ ጉልበታቸውንና ገንዘባቸውን ተጠቅመው ከአምላክ መንግሥት ጋር የተያያዙ ጉዳዮችን በማራመድ ለይሖዋ መሥዋዕት የማቅረብ መብት አላቸው። ካሉን ነገሮች መካከል ምርጡን ለይሖዋ መሥዋዕት አድርገን በማቅረብ እሱን የማምለክ መብታችንን ከፍ አድርገን እንደምንመለከተው እናሳያለን። ሐዋርያው ጳውሎስ ፈጽሞ ችላ ልንላቸው የማይገቡ የተለያዩ የአምልኳችንን ገጽታዎች ጠቅሷል። (ዕብ. 10:22-25) ከእነዚህ መካከል ወደ ይሖዋ በጸሎት መቅረብ፣ ተስፋችንን በይፋ ማወጅ፣ በጉባኤ ደረጃ አንድ ላይ መሰብሰብ እንዲሁም “[የይሖዋ ቀን] እየቀረበ መምጣቱን ስናይ ከበፊቱ ይበልጥ” እርስ በርስ መበረታታት ይገኙበታል። በራእይ መጽሐፍ መደምደሚያ አካባቢ የይሖዋ መልአክ ሁለት ጊዜ “ለአምላክ ስገድ!” ብሏል፤ ይህም ይሖዋን የማምለክን አስፈላጊነት ጎላ አድርጎ ያሳያል። (ራእይ 19:10፤ 22:9) ታላቁን የይሖዋ መንፈሳዊ ቤተ መቅደስ አስመልክቶ ያገኘነውን ጥልቅ መንፈሳዊ እውነት እንዲሁም ያለንን ታላቁን አምላካችንን ይሖዋን የማምለክ ውድ መብት ፈጽሞ ልንረሳው አይገባም! w23.10 29 አን. 17-18