ዓርብ፣ መስከረም 12
የዚህ ዓለም ትእይንት እየተለዋወጠ ነው።—1 ቆሮ. 7:31
ምክንያታዊ ነው የሚል ስም አትርፉ። ራሳችሁን እንዲህ እያላችሁ ጠይቁ፦ ‘ሰዎች ምክንያታዊ፣ እሺ ባይና ሰው የሚለኝን የምሰማ እንደሆንኩ ይሰማቸዋል? ወይስ ድርቅ ያልኩ፣ ግትርና አልሰማም ባይ አድርገው ይመለከቱኛል? ሌሎችን ለማዳመጥ፣ የሚቻል ከሆነም ሐሳባቸውን ለመቀበል ፈቃደኛ ነኝ?’ ይበልጥ ምክንያታዊ በሆንን መጠን ይሖዋንና ኢየሱስን ይበልጥ እንመስላለን። ምክንያታዊ መሆን፣ ለውጦች ሲያጋጥሙን ሁኔታዎችን እንደአመጣጣቸው ለማስተናገድ ያስችለናል። አንዳንድ ጊዜ ለውጦች ባልጠበቅነው አቅጣጫ ሕይወታችንን ሊያከብዱብን ይችላሉ። በድንገት ከባድ የጤና ችግር ሊያጋጥመን ይችላል፤ ወይም በምንኖርበት አካባቢ በኢኮኖሚው አሊያም በፖለቲካው ሥርዓት ላይ ድንገተኛ ለውጥ ተከስቶ ኑሯችን ሊመሰቃቀልብን ይችላል። (መክ. 9:11) የአገልግሎት ምድብ ለውጥ እንኳ ፈተና የሚሆንበት ጊዜ አለ። የሚከተሉትን አራት እርምጃዎች ከወሰድን አዲሱን ሁኔታ መልመድ ቀላል ይሆንልናል፦ (1) እውነታውን መቀበል፣ (2) ነገን አሻግሮ ማየት፣ (3) በጎ በጎውን ማሰብ እንዲሁም (4) ሌሎችን መርዳት። w23.07 21-22 አን. 7-8
ቅዳሜ፣ መስከረም 13
አንተ እጅግ የተወደድክ ነህ።—ዳን. 9:23
ነቢዩ ዳንኤል በባቢሎናውያን ተማርኮ ወደ ሩቅ አገር በተወሰደበት ወቅት ገና ወጣት ነበር። ዳንኤል ልጅ ቢሆንም የባቢሎን ባለሥልጣናት በጣም ተደመሙበት። እነሱ ያዩት ‘ውጫዊ ገጽታውን’ ማለትም ‘እንከን የሌለበት፣ መልከ መልካም’ እና ከታዋቂ ቤተሰብ የመጣ መሆኑን ነው። (1 ሳሙ. 16:7) በመሆኑም ባቢሎናውያን በቤተ መንግሥቱ ውስጥ እንዲያገለግል አሠለጠኑት። (ዳን. 1:3, 4, 6) ይሖዋ ዳንኤልን የወደደው ምን ዓይነት ሰው ለመሆን እንደመረጠ ስላየ ነው። እንዲያውም ይሖዋ ዳንኤልን ለበርካታ አሥርተ ዓመታት እሱን በታማኝነት ካገለገሉት ከኖኅና ከኢዮብ ጋር አብሮ የጠቀሰው ዳንኤል ገና በአሥራዎቹ ዕድሜ መጨረሻ ወይም በሃያዎቹ ዕድሜ መጀመሪያ ሳለ ሊሆን ይችላል። (ዘፍ. 5:32፤ 6:9, 10፤ ኢዮብ 42:16, 17፤ ሕዝ. 14:14) ደግሞም ዳንኤል ባሳለፈው ረጅምና አስደናቂ ሕይወት በሙሉ ይሖዋ ይወደው ነበር።—ዳን. 10:11, 19፤ w23.08 2 አን. 1-2
እሁድ፣ መስከረም 14
ስፋቱ፣ ርዝመቱ፣ ከፍታውና ጥልቀቱ ምን ያህል እንደሆነ [በሚገባ ተረዱ]።—ኤፌ. 3:18
አንድን ቤት ለመግዛት ስታስብ የምትገዛውን ቤት ከሁሉም አቅጣጫ በአካል በደንብ ማየት እንደምትፈልግ ምንም ጥያቄ የለውም። መጽሐፍ ቅዱስን ስናነብና ስናጠናም ተመሳሳይ ነገር ማድረግ እንችላለን። በጥድፊያ ካነበብከው፣ የምትማረው “የአምላክን ቅዱስ መልእክት መሠረታዊ ነገሮች” ብቻ ነው። (ዕብ. 5:12) ከዚህ ይልቅ ልክ እንደ ቤቱ ሁሉ ወደ ውስጥ ገብተህ ዝርዝር መረጃዎችን ለመመርመር ጥረት አድርግ። መጽሐፍ ቅዱስን ማጥናት የምትችልበት አንዱ ግሩም መንገድ በውስጡ ያሉት መልእክቶች እንዴት እንደሚያያዙ ማስተዋል ነው። የምታምንባቸውን እውነቶች ምንነት ብቻ ሳይሆን በእነዚህ እውነቶች የምታምነው ለምን እንደሆነም ለመመርመር ጥረት አድርግ። የአምላክን ቃል በሚገባ ለመረዳት ጥልቀት ያላቸውን የመጽሐፍ ቅዱስ እውነቶች መማር ይኖርብናል። ሐዋርያው ጳውሎስ ክርስቲያን ወንድሞቹና እህቶቹ የእውነት ‘ስፋት፣ ርዝመት፣ ከፍታና ጥልቀት ምን ያህል እንደሆነ በሚገባ መረዳት እንዲችሉ’ የአምላክን ቃል በትጋት እንዲያጠኑ አበረታቷቸዋል። እንዲህ ካደረጉ በእምነታቸው ይበልጥ ‘ሥር መስደድና መታነጽ’ ይችላሉ። (ኤፌ. 3:14-19) እኛም ይህንኑ ልናደርግ ይገባል። w23.10 18 አን. 1-3