የመንግሥቱ አዋጅ ነጋሪዎች ሪፖርት
“ብርሃናችሁ . . . በሰው ፊት ይብራ”
ኢየሱስ በተራራ ስብከቱ ላይ ደቀ መዛሙርቱን “እናንተ የዓለም ብርሃን ናችሁ” ብሏቸው ነበር። አክሎም “መልካሙን ሥራችሁን አይተው በሰማያት ያለውን አባታችሁን እንዲያከብሩ ብርሃናችሁ እንዲሁ በሰው ፊት ይብራ” በማለት አሳስቧቸዋል።— ማቴዎስ 5:14-16
ኢጣሊያ የሚገኙ የይሖዋ ምሥክሮች የሚያሳዩት መልካም ባሕርይ በሰዎች ዘንድ ሳይስተዋል አልቀረም። ለምሳሌ ያህል በዓመታዊው የአውራጃ ስብሰባዎቻቸው ላይ ያሳዩት የታረመ ጠባይ ቀጥሎ የቀረበው ዘገባ እንደሚያሳየው ለአምላክ ውዳሴ አምጥቷል:-
▪ በተርኒ ኢጣሊያ የምትኖር አንዲት ሴት እዚህ ከተማ በሚገኘው ስታዲዮም አቅራቢያ ባለው ቡና ቤት ተቆጣጣሪ በመሆን ለብዙ ዓመታት ልጅዋን ረድታታለች። እንዲህ ትላለች:- “የእግር ኳስ ግጥሚያ ለመመልከት በሚመጡትና በይሖዋ ምሥክሮች ስብሰባ ላይ በሚገኙት ልዑካን መካከል ከፍተኛ ልዩነት እንዳለ ተመልክቼአለሁ። ምሥክሮቹ በአለባበሳቸው ልከኞች ከመሆናቸውም በላይ ታማኞችና ሰው አክባሪ ናቸው። የተለያየ ዓይነት ዘር ያላቸው ሰዎች እንዴት እንዲህ ያለ ስምምነት ሊኖራቸው ቻለ እያልኩ ዘወትር ራሴን እጠይቅ ነበር።
“አንድ ቀን አንዲት ምሥክር መንገድ ላይ አስቆመችኝና የአምላክን ስም አውቅ እንደሆነ ጠየቀችኝ። እኔም እንደማላውቅ ገልጬላት የይሖዋ ምሥክሮች ጥሩ ሰዎች እንደሆኑ አውቅ ስለነበር መጥታ ብታነጋግረኝ ፈቃደኛ መሆኔን ነገርኳት። ሙታን በምን ዓይነት ሁኔታ እንደሚገኙ የነበሩኝን ጥያቄዎች ከመጽሐፍ ቅዱስ መለሰችልኝ። ያለ ምንም ማመንታት የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት እንዲደረግልኝ ተስማማሁ። ከሁለት ሳምንት በኋላም በስብሰባዎች ላይ መገኘት ጀመርኩ።
“በመጀመሪያ ልጄ ትቃወመኝ ጀመር። ይሁን እንጂ የማሳየው ጠባይና ቁርጠኝነት አመለካከቷን እንድትለውጥ አደረጋት። የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት ከጀመርኩ ዘጠኝ ወራት አልፈውኛል። በአሁኑ ጊዜ ሴት ልጄና ባለቤቷ ቡና ቤታቸው ስለሚመጡት ምሥክሮች የአድናቆት ቃላት ይናገራሉ። እኔም በዚሁ ስታዲዮም በተደረገ ትልቅ ስብሰባ ላይ ተጠምቄአለሁ።”
▪ ሮዜቶ ዴልዪ አብሩትሲ ከተማ የተደረገው የአውራጃ ስብሰባ ከተጠናቀቀ በኋላ አንድ የመዝናኛ ቦታ አስተዳዳሪ ስለ ተመለከቱት ነገር አስተያየታቸውን ሲሰጡ እንዲህ ብለዋል:- “የይሖዋ ምሥክሮች በሚያደርጉት ነገር ሁሉ ታማኝ እንደሆኑ ተገንዝቤአለሁ። ባለፈው ሳምንት 40 የይሖዋ ምሥክሮች ወደ መዝናኛ ቦታዬ መጥተው ነበር። እዚያም ምንም ዓይነት ችግር አልፈጠሩም። እንዲያውም በተሳቢ ክፍላቸው ወይም በድንኳኖቻቸው ውስጥ ትርፍ ሰው ካለ መጥተው የሚነግሯችሁ እነርሱ ብቻ ናቸው። እንደእኔ አመለካከት ከሁሉም የተሻሉ ደንበኞች ሊሆኗችሁ የሚችሉት እነርሱ ብቻ ናቸው።”
▪ ይኸው የአውራጃ ስብሰባ ከተከናወነ በኋላ አንድ የሆቴል አስተዳዳሪ እንዲህ በማለት ተናግረዋል:- “የይሖዋ ምሥክሮች በጠቅላላ ሰላማውያን ናቸው። አይረብሹም። በጊዜ ክፍላቸው ገብተው ይተኛሉ። በእርግጥም ደጎች፣ ታማኞችና የታረመ ጠባይ ያላቸው ናቸው። ሁሉም ሰው እንደነርሱ ቢሆን ኖሮ በጣም ያስደስት ነበር። ሌሎች ሰዎች ያገኙትን ሁሉ ያበባ ማስቀመጫዎችን፣ የሲጋራ መተርኮሻዎችንና የሽንት ቤት ወረቀትና ስኳር እንኳን ሳይቀር ይሰርቃሉ! እናንተ ግን እንዲህ ያለ ነገር አድርጋችሁ አታውቁም። ምሽት ላይ ልጆቻችሁ ከማቀዝቀዣ ውስጥ አይስ ክሬም በሚወስዱበት ጊዜ ምን ያህል እንደወሰዱ ለማወቅ ሄጄ ማረጋገጥ አያስፈልገኝም። ምን ያህል ዕዳ እንዳለባቸው ያሰሉና ወዲያው መጥተው ይከፍላሉ። በእነርሱ ላይ ከፍተኛ እምነት አለኝ። ሌሎችም እንደነርሱ ቢሆኑ እንዴት ጥሩ ይሆን ነበር! እንግዶቼ ሁሉ የይሖዋ ምሥክሮች ቢሆኑ ደስ ይለኝ ነበር።”
እንደ ሌሎች አገሮች ሁሉ በኢጣሊያ የሚገኙ የይሖዋ ምሥክሮችም በሰዎች ዘንድ በደንብ የታወቁ ናቸው። ‘በአሕዛብ መካከል ጥሩ ጠባይ ያሳያሉ።’ ይህ ባሕርያቸው ስሙን ለተሸከሙት ለእውነተኛው አምላክ ውዳሴ ያመጣል።—1 ጴጥሮስ 2:12