የ“ትራየሩ ቅዱስ ካባ”
ትራየር 2,000 ዓመት የሚጠጋ ታሪክ ያላት በጀርመን የምትገኝ ጥንታዊ ከተማ ናት።a ትራየር ከካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን ጋር ለብዙ መቶ ዘመናት የቆየ ጠንካራ ትስስር አላት። በ1996 በትራየር የሚገኘው ካቴድራል ከከተማዋ ጋር እኩል እድሜ አለው ተብሎ የሚታመን አንድ ቅርስ ለሕዝብ አሳይቶ ነበር። ይህ ቅርስ የትራየሩ ቅዱስ ካባ ይባላል።
ካባው 1.57 ሜትር ቁመትና 1.09 ሜትር ስፋት ያለው ሲሆን እጅጌው ጉርድ ነው። ካባው ከጥጥ የተሠራ ሲሆን ሃንስ-ዮአኪም ካን ወደ ትራየርና አካባቢው ለሚጓዙ ጎብኚዎች የሚሆን መመሪያ (ጀርመንኛ) በተባለው መጽሐፋቸው ላይ ካባው ይለበስ የነበረው ከላይ ሳይሆን አይቀርም በማለት ተናግረዋል። በቆየባቸው ረዥም ዘመናት ውስጥ አብዛኛው የልብሱ ክፍል በቁርጥራጭ ጨርቆች ተጠግኗል እንዲሁም ተጥፏል። አንዳንዶች ልብሱ ለመጀመሪያ ጊዜ የተሠራው በሁለተኛው ወይም በመጀመሪያው መቶ ዘመን እዘአ ሳይሆን አይቀርም ይላሉ። ይህ ጊዜ ትክክል ከሆነ ካባው ውድ የሙዚየም ቅርስ ነው ማለት ነው።
ይሁን እንጂ አንዳንዶች ልብሱ ውድ ብቻ ሳይሆን ቅዱስም ነው ይላሉ። በዚህም የተነሳ ቅዱስ ካባ ብለው ሰይመውታል። እንዲህ የሚሉት ልብሱ ኢየሱስ ክርስቶስ ከውስጥ ይለብሰው እንደነበረው ዓይነት ልብስ ምንም ስፌት ሳይኖረው አንድ ወጥ ሆኖ በመሠራቱ ነው። (ዮሐንስ 19:23, 24) እንዲያውም አንዳንዶች “ቅዱሱ ካባ” መሲሑ ይለብሰው የነበረው ልብስ ነው በማለት ይናገራሉ።
ካባው ወደ ትራየር እንዴት እንደመጣ አይታወቅም። አንድ የማመሳከሪያ ጽሑፍ ካባውን “ወደ እዚህ ከተማ ያመጣችው የታላቁ ቆስጠንጢኖስ እናት ንግሥት ሄለና ናት” ይላል። ካን ቅርሱ በትራየር እንደሚገኝ ለመጀመሪያ ጊዜ አስተማማኝ ዘገባ የቀረበው በ1196 ጀምሮ ነው በማለት ገልጸዋል።
በካቴድራሉ ውስጥ የተቀመጠው ይህ ካባ ከ16ኛው መቶ ዘመን ጀምሮ ሰዎች እንዲያዩት አልፎ አልፎ ይወጣ ነበር። ለምሳሌ በትራየር ላይ ከፍተኛ ውድመት ያስከተለው የሠላሳ ዓመቱ ጦርነት ካበቃ ከጥቂት ጊዜ በኋላ ማለትም በ1655 ለሕዝብ ታይቶ ነበር። ቀስ በቅስ ካባውን ለማየት ለሚጓዙ ሰዎች ቅርሳ ቅርሶችን መሸጥ ከፍተኛ ገቢ የሚያስገኝ እየሆነ መጣ።
በዚህ መቶ ዘመን በ1933፣ በ1959 እና በ1996 ሦስት የ“ቅዱስ ካባ” ጉዞዎች ተደርገዋል። በ1933 ካባውን ለመመልከት ጉዞ እንደሚደረግ የተገለጸው ሂትለር በጀርመን ራይክ ቻንስለር ሆኖ በተመረጠበት ቀን ነበር። እነዚህ ሁለት ክስተቶች መገጣጠማቸው ለጉዞው ከፍተኛ ድምቀት ሰጥቶታል በማለት ካን ይናገራሉ። የደንብ ልብስ የለበሱ የናዚ ወታደሮች ከካቴድራሉ ውጭ ያሉትን ተጓዦች በሰልፍ አጅበዋቸዋል። በዚያ ዓመት ሁለት ሚልዮን ተኩል የሚያክሉ ሰዎች ካባውን ተመልክተዋል።
በትራየር ለረዥም ዓመታት የኖሩት ኸርበርት የተባሉ አንድ ሰው በ1959 የተደረገውን ጉዞ በ1996 ከተደረገው ጉዞ ጋር በማነጻጸር እንዲህ ብለዋል:- “በ1959 መንገዶች በሰዎችና በየቦታው ቅርሳ ቅርስ በሚሸጡ ነጋዴዎች ተጨናንቀው ነበር። በዚህ ዓመት ግን ሁሉም ነገር ጸጥታ የሰፈነበት ሆኗል” ብለዋል። በእርግጥም በ1996 ካባውን የተመለከቱት ሰዎች ቁጥር 700,000 ብቻ ሲሆኑ በ1959 ከነበሩት ሰዎች በአንድ ሚልዮን ያነሱ ነበሩ።
ካባውን ለመመልከት የሚሄዱት ለምንድን ነው?
ቤተ ክርስቲያኒቱ ካባው የአምልኮ ምልክት ተደርጎ መታየት የለበትም በማለት አጥብቃ ትናገራለች። ምንም ዓይነት ስፌት ሳይኖረው አንድ ወጥ ሆኖ የተሠራው ካባ የሚታየው የቤተ ክርስቲያን የአንድነት ምልክት ተደርጎ ነው። ፍራንክፈርተር አልጌሚን ዘይቱንግ እንደዘገበው ካባውን ለመመልከት ጉዞ እንደሚደረግ መግለጫ በወጣበት ጊዜ ሽፔታል የተባሉ ጳጳስ እንዲህ ብለዋል:- “በዓለማችን ያለው ያልተለመደ ሁኔታ እኛ ክርስቲያኖች ያልተለመዱ መልሶች እንድንሰጥ ተጽዕኖ ያሳድሩብናል። እየጨመረ የመጣውን ጥላቻ፣ ጭካኔና ዓመፅ መቃወም አለብን።” አንድ ሰው ካባውን መመልከቱ አንድነትን እንዲያስታውስ ያደርገዋል በማለት ጳጳሱ አብራርተዋል።
ይሁን እንጂ አንድ ሰው የቤተ ክርስቲያንን አንድነት እንዲያስታውስ “ቅዱስ ካባ” የሚያስፈልገው ለምንድን ነው? ካባው ቢበላሽ ወይም ቢቀዳደድ ወይም ውሸት እንደሆነ ተደርጎ ቢነገር ምን ነገር ሊከሰት ይችላል? የቤተ ክርስቲያኑ አንድነት ይናጋል ማለት ነው? ካባውን ለመመልከት ወደ ትራየር መሄድ የማይችሉ ሰዎችስ? በቤተ ክርስቲያኑ ውስጥ ላለው አንድነት ምንም ደንታ የላቸውም ማለት ነው?
የጥንት ክርስቲያኖች የክርስቲያናዊ አንድነትን አስፈላጊነት የሚያስታውሳቸው ምልክት እንደነበራቸው የሚገልጽ ምንም ዓይነት ቅዱስ ጽሑፋዊ ፍንጭ የለም። ከዚህ ይልቅ ሐዋርያው ጳውሎስ “በእምነት እንጂ በማየት አንመላለስምና” በማለት ክርስቲያኖችን አሳስቧቸዋል። (2 ቆሮንቶስ 5:6) ስለዚህ እውነተኛ ክርስቲያኖች ያላቸው አንድነት ‘የእምነት አንድነት’ ተብሎ ሊገለጽ ይችላል።— ኤፌሶን 4:11-13
[የግርጌ ማስታወሻ]