መቅረትህ ያጎድላል!
1 አልፎ አልፎ ከጉባኤ ስብሰባዎች እንቀር ይሆናል። በዚህ ጊዜ ‘እኔ ቀረሁ አልቀረሁ ጨርሶ የሚያስታውሰኝም ሰው የለም’ ብለን ልናስብ እንችላለን። ይህ አስተሳሰብ ትክክል አይደለም! ማንኛውም የሰውነታችን ክፍል የሚያበረክተው ድርሻ እንዳለ ሁሉ እያንዳንዳችን በጉባኤ ውስጥ ጠቃሚ ድርሻ እናበረክታለን። (1 ቆሮ. 12:12) ከአንዱ ሳምንታዊ ስብሰባ መቅረታችን ስብሰባው ላይ የተገኙትን የሌሎችን መንፈሳዊ ደኅንነት ሊጎዳ ይችላል። በጉባኤ ስብሰባ ላይ መቅረትህ እንደሚያጎድል ምንም አትጠራጠር!
2 የምታበረክተው ጠቃሚ ድርሻ፦ ጳውሎስ ከወንድሞቹ ጋር ለመሰብሰብ ይናፍቅ ነበር። ለምን እንደዚህ እንደተሰማው ሲገልጽ በሮሜ 1:11, 12 ላይ እንዲህ ብሏል:- “ትጸኑ ዘንድ መንፈሳዊ ስጦታ እንዳካፍላችሁ . . . በመካከላችን ባለች በእናንተና በእኔ እምነት አብረን በእናንተ እንድንጽናና ነው።” በተመሳሳይም በጉባኤ ስብሰባዎች ላይ በምንሰጣቸው ሐሳቦችና በምናቀርባቸው ክፍሎች ሌላው ቀርቶ በዚያ በመገኘታችን ብቻ እንኳ በታማኝነት ጎዳና ለመቀጠል በሚያስችል መንገድ እርስ በርስ ለመተናነጽ የበኩላችንን አስተዋጽኦ እናደርጋለን።—1 ተሰ. 5:11
3 በጉባኤ ስብሰባዎች ላይ ሌሎችን ለማግኘት አትጓጓምን? የሚሰጡትን ሐሳብ በጥሞና አዳምጥና እምነታቸውን በቃላት ሲገልጹ አድንቅ። መንፈሳዊ ስጦታዎቻቸው ላንተ መታነጽ አስተዋጽኦ ያበረክታሉ። እነዚህ ወንድሞችና እህቶች ከስብሰባ ቀርተው ቢሆን ኖሮ መቅረታቸው በጣም እንዳጎደለ ይሰማህ ነበር። አንተ ስትቀርም ወንድሞችህና እህቶችህ ተመሳሳይ የሆነ ስሜት ይሰማቸዋል።
4 ስብሰባዎች የሚያበረክቱት ጠቃሚ ድርሻ፦ ስብሰባዎች ለመንፈሳዊ ደኅንነታችን ምን ያህል ጠቃሚ እንደሆኑ ሲገልጽ መጠበቂያ ግንብ በአንድ ወቅት እንዲህ ብሏል:- “በዚህ በሁከት በተሞላና ሥነ ምግባር በጎደለው ዓለም ውስጥ የክርስቲያን ጉባኤ ትክክለኛ መንፈሳዊ መጠለያ ነው። . . . ፍቅርና ሰላም የሰፈነበት ቦታ ነው። ስለዚህ በሁሉም የጉባኤ ስብሰባዎች ላይ አዘውታሪ ተሰብሳቢ ሁን።” (መጠበቂያ ግንብ 93 8/15 11) መንፈሳዊነታችንን የሚያዳክሙ ሁኔታዎችን በየቀኑ እንጋፈጣለን። ካልተጠነቀቅን በግል ጭንቀቶቻችን ከመዋጣችን የተነሳ ይበልጥ አስፈላጊ የሆኑ መንፈሳዊ ጉዳዮችን ልንዘነጋ እንችላለን። በይሖዋ አገልግሎት በአንድነትና በቅንዓት ለመቀጠል እንድንችል የሚያስፈልገንን ማበረታቻ ለማግኘት አንዳችን በሌላው ላይ ጥገኞች ነን።—ዕብ. 10:24, 25
5 ስብሰባ መገኘታችን እጅግ አስፈላጊ ነገር ነው። አልፎ አልፎ ሕመምና ያልተጠበቀ አጋጣሚ ከስብሰባ ያስቀረን ይሆናል። ከዚህ በተረፈ ግን ይሖዋን በኅብረት ከሚያወድሱት ብዙ ሰዎች መካከል ሁልጊዜ ለመገኘት ቁርጥ ውሳኔ እናድርግ!—መዝ. 26:12