በድፍረት ትሰብካላችሁን?
1 ጴጥሮስና ዮሐንስ ተቃዋሚዎች ቢያስሯቸውና ቢያስፈራሯቸውም የመንግሥቱን መልእክት በድፍረት መስበካቸውን አላቋረጡም። (ሥራ 4:17, 21, 31) ለእኛስ በድፍረት መስበክ ማለት ምን ትርጉም አለው?
2 በድፍረት መመሥከር:- “ደፋር” ለሚለው ቃል ተመጣጣኝ የሆነው ሐረግ “መንፈሰ ጠንካራነት” ሲሆን “ቆራጥነት፣ ጠንካራነት እና ጽናት” የሚል ትርጉም አለው። ለእውነተኛ ክርስቲያኖች፣ በድፍረት መስበክ ማለት ምሥራቹን ለሌሎች ለማካፈል የሚያስችል አጋጣሚ በሚገኝበት ጊዜ ሁሉ ከመናገር አለመፍራት ማለት ነው። (ሥራ 4:20፤ 1 ጴጥ. 3:15) በሌላ አነጋገር በምሥራቹ አለማፈርን ያመለክታል። (መዝ. 119:46፤ ሮሜ 1:16፤ 2 ጢሞ. 1:8) ስለሆነም ድፍረት በዚህ የመጨረሻ ዘመን የመንግሥቱን ምሥራች እንድንሰብክ የተሰጠንን ተልዕኮ ለመፈጸም የሚያስፈልግ ባሕርይ ነው። ይህ ባሕርይ ሰዎችን በምናገኝበት ሥፍራ ሁሉ ምሥራቹን እንድናካፍላቸው ይገፋፋናል።—ሥራ 4:29፤ 1 ቆሮ. 9:23
3 ድፍረት በትምህርት ቤት:- ፍርሃት ትምህርት ቤት አብረውህ ለሚማሩ እንዳትሰብክ እንቅፋት ይሆንብሃልን? አንዳንድ ጊዜ ሁኔታው ቀላል አይደለም፤ እንዲያውም ፈታኝ ሊሆን ይችላል። ይሁን እንጂ ለሌሎች መስበክ የሚያስችል ድፍረት እንዲሰጥህ ከጸለይክ ይሖዋ ብርታት ይሰጥሃል። (መዝ. 138:3) ድፍረት የይሖዋ ምሥክር መሆንህን ሌሎች እንዲያውቁ እንድታደርግና የሚያጋጥምህን ፌዝ እንድትቋቋም ይረዳሃል። በዚህም ምክንያት በትምህርት ቤት መስበክህ የሚሰሙህን ሊያድን ይችላል።—1 ጢሞ. 4:16
4 ድፍረት በሥራ ቦታ:- በሥራ ቦታ ሌሎች የይሖዋ ምሥክር መሆንህን ያውቃሉ? የሥራ ባልደረቦችህ ምሥራቹ ሊደርሳቸው የሚችለው አንተ ከሰበክላቸው ብቻ ሊሆን ይችላል። እንዲሁም ድፍረት በጉባኤ ስብሰባዎችና በትላልቅ ስብሰባዎች ላይ ለመገኘት ፈቃድ እንድታገኝ ይረዳሃል።
5 ድፍረት ፈተና ሲያጋጥም:- ተቃውሞ ሲያጋጥም ድፍረት ማሳየት በጣም ወሳኝ የሆነ ጉዳይ ነው። (1 ተሰ. 2:1, 2) ዛቻ፣ ፌዝ ወይም ቀጥተኛ ስደት በሚያጋጥመን ጊዜ እምነታችንን አጥብቀን እንድንይዝ ይረዳናል። (ፊልጵ. 1:27, 28) አምላካችን ይሖዋ ያስቀመጠልንን የአቋም ደረጃ ከመጠበቅ ወደኋላ እንድንል የሚያደርግ ተጽዕኖ በሚያጋጥመን ጊዜ ጸንተን እንድንቆም ያጠነክረናል። ሌሎች ሰዎች ጠብ ለመጫር በሚፈልጉበት ጊዜ ሰላማውያን ሆነን እንድንገኝ ያበረታናል።—ሮሜ 12:18
6 በግለሰብ ደረጃ ምንም ዓይነት ችግር ቢያጋጥመን ምሥራቹን በድፍረት መስበካችንን እንቀጥል።—ኤፌ. 6:18-20