የጥያቄ ሣጥን
◼ በቲኦክራሲያዊ የአገልግሎት ትምህርት ቤትና በአገልግሎት ስብሰባ ላይ እያንዳንዱ ክፍል ከቀረበ በኋላ ማጨብጨብ ተገቢ ነው?
ፈጣሪያችን ይሖዋ ምድርን በመሠረተበት ወቅት ‘የንጋት ከዋክብት እንደዘመሩና መላእክትም እልል እንዳሉ’ መጽሐፍ ቅዱስ ይናገራል። (ኢዮብ 38:7) እነዚህ መላእክት የይሖዋ ጥበብ፣ ጥሩነቱና ኃይሉ ለየት ባለ መንገድ ለተንጸባረቀበት ድንቅ የፍጥረት ሥራው እሱን ለማወደስ ፈልገው ነበር።
እኛም ወንድሞቻችን ላደረጉት ጥረትም ሆነ ላቀረቡት ክፍል ያለንን ልባዊ አድናቆት መግለጻችን ተገቢ ነው። ለምሳሌ ያህል እንደ ልዩ፣ ወረዳና አውራጃ በመሳሰሉ ትላልቅ ስብሰባዎች ላይ ንግግሮች እና የተለያዩ ክፍሎች ሲቀርቡ እናጨበጭባለን። ወንድሞች በእነዚህ ስብሰባዎች ላይ ክፍሎችን ተዘጋጅተው ለማቅረብ ተጨማሪ ጊዜና ጥረት ጠይቆባቸዋል። እንዲህ ባሉ አጋጣሚዎች ማጨብጨባችን ተናጋሪው ላደረገው ከፍተኛ ጥረት አድናቆት እንዳለን ከማሳየቱም በተጨማሪ ይሖዋ በቃሉና በድርጅቱ በኩል የሰጠንን መመሪያዎች እንደምናደንቅ የሚያመለክት ነው።—ኢሳ. 48: 17፤ ማቴ. 24:45-47
ታዲያ በቲኦክራሲያዊ የአገልግሎት ትምህርት ቤትና በአገልግሎት ስብሰባ ላይ ለሚቀርቡ ክፍሎች ማጨብጨብን በተመለከተ ምን ለማለት ይቻላል? አንድ ተማሪ ለመጀመሪያ ጊዜ ክፍል አቅርቦ ሲወርድ ወይም በሌሎች አጋጣሚዎች አድናቆታችንን በጭብጨባ እንዳንገልጽ የሚከለክል ሕግ የለም። ይሁን እንጂ እንዲህ የምናደርገው እንዲያው በዘልማድ ከሆነ ጭብጨባ ትርጉሙን ያጣል። በመሆኑም እያንዳንዱ ክፍል ከቀረበ በኋላ አናጨበጭብም።
ምንም እንኳ በቲኦክራሲያዊ የአገልግሎት ትምህርት ቤትና በአገልግሎት ስብሰባ ላይ ክፍል ከቀረበ በኋላ በአብዛኛው የማናጨበጭብ ቢሆንም ሁላችንም፣ ላገኘናቸው መመሪያዎችና ወንድሞች ላደረጉት ጥረት ያለንን አድናቆት መግለጽ የምንችልባቸው ሌሎች መንገዶች አሉ። ወንድሞች ክፍሉን አቅርበው እስኪጨርሱ ድረስ ንቁ በመሆንና ትኩረት ሰጥተን በመከታተል ይህን ማድረግ እንችላለን። በተጨማሪም ስብሰባው እንዳለቀ በግል ቀርበን ላደረጉት ጥረት አድናቆታችንን መግለጽ እንችላለን።—ኤፌ. 1:15, 16