ለይሖዋ ቀን የተዘጋጃችሁ ሁኑ
ከአንደኛ ተሰሎንቄ የተገኙ ዋና ዋና ነጥቦች
የይሖዋ ቀን! በጥንትዋ ተሰሎንቄ ይኖሩ የነበሩ ክርስቲያኖች በጣም የቀረበ መስሎአቸው ነበር። ግን እነርሱ ትክክል ነበሩን? የይሖዋ ቀን የሚመጣው መቼ ነው? ሐዋርያው ጳውሎስ በቆሮንቶስ ሆኖ በ50 እ.ዘ.አ. አካባቢ ለተሰሎንቄ ክርስቲያኖች በጻፈው የመጀመሪያ ደብዳቤ ያስገነዘበው ዋነኛ ቁም ነገር ይህ ነበር።
የሮማ ግዛት የመቄዶንያ ክፍለ ግዛት የአስተዳደር ዋና ከተማ በነበረችው በተሰሎንቄ የነበረውን ጉባዔ ያቋቋሙት ጳውሎስና ሲላስ ነበሩ። (ሥራ 17:1-4) ጳውሎስ ለተሰሎንቄ ጉባዔ በጻፈው ደብዳቤ ላይ ምሥጋና፣ ምክርና ስለ ይሖዋ ቀን የሚገልጽ ትምህርት ልኮላቸዋል። እኛም በተለይ የይሖዋ ቀን በጣም ቅርብ በሆነበት በዚህ ዘመን ከዚህ ደብዳቤ ብዙ ጥቅም ልናገኝ እንችላለን።
ማመስገንና ማበረታታት
ጳውሎስ በመጀመሪያ የተሰሎንቄን ሰዎች አመሰገናቸው። (1ተሰ 1:1-10) ምሥጋና የተገባቸው ስለ ጽናታቸውና ስለ ታማኝነት ሥራቸው ነበር። በተጨማሪም “ቃሉን በብዙ መከራ ከመንፈስ ቅዱስ ደስታ ጋር” ስለተቀበሉ መመስገን የሚገባቸው ነበሩ። አንተስ እንደ ጳውሎስ ሌሎችን ታመሰግናለህን?
ሐዋርያው ጥሩ ምሳሌ ትቶላቸው ነበር። (2:1-12) በፊሊጲ ብዙ መከራ ቢደርስበትም ለተሰሎንቄ ሰዎች ምሥራቹን ለመናገር ከአምላክ ድፍረት አግኝቶ ነበር። ከከንቱ ውዳሴ፣ ከመጎምጀትና ከበሬታ ከመፈለግ ይሸሽ ነበር። በመካከላቸው በነበረበትም ጊዜ ለልጆችዋ እንደምትንከባከብ ሞግዚት ሆነ እንጂ ሸክም አልሆነባቸውም። በዛሬ ዘመን ለሚኖሩ ሽማግሌዎች እንዴት ያለ ጥሩ ምሳሌ ነው!
ጳውሎስ ቀጥሎ የተናገራቸው ቃላት የተሰሎንቄ ክርስቲያኖች በሚሰደዱበት ጊዜ ጸንተው እንዲቆሙ የሚያበረታቱ ናቸው። (2:13 እስከ 3:13) የአገራቸው ሰዎች ባደረሱባቸው ስደት ሁሉ ጸንተዋል። ጢሞቴዎስም በጥሩ መንፈሣዊ ሁኔታ እንደሚገኙ የሚገልጽ ዜና ለጳውሎስ አምጥቶለት ነበር። ሐዋርያው በፍቅር እንዲበዙና ልባቸውም እንዲጸና ጸለየ። የይሖዋ ምሥክሮችም በተመሳሳይ ለሚሰደዱ የእምነት ባልደረቦቻቸው ይጸልያሉ፤ ከተቻላቸው ያበረታቷቸዋል፤ ስለ ታማኝነታቸው በሚገልጹ ዜናዎችም ይደሰታሉ።
በመንፈሣዊ ንቁ ሆኖ መኖር
ከዚህ ቀጥሎ የተሰሎንቄ ክርስቲያኖች ምክር ተሰጣቸው። (4:1-18) በበለጠ ሁኔታ አምላክን በሚያስደስት መንገድ መመላለስ ነበረባቸው። በይበልጥ የወንድማማች ፍቅር ማሳየትና ለኑሮ የሚያስፈልጋቸውን ለማግኘት በእጆቻቸው መሥራት ነበረባቸው። ኢየሱስ በሚገኝበት ጊዜ ሞተው የነበሩ በመንፈስ የተወለዱ አማኞች በመጀመሪያ ከሙታን ተነስተው ከኢየሱስ ጋር እንደሚተባበሩ ተስፋ በማድረግ እርስ በርሳቸው መጽናናት ነበረባቸው። በኋላም በሕይወት የቆዩት ቅቡዓን ከክርስቶስና ሞተው ከተነሱ በኋላ ቀደም ብለው ሰማያዊ ትንሣዔ ካገኙት ጋር ይተባበራሉ።
ጳውሎስ ከዚህ ቀጥሎ ስለ ይሖዋ ቀን ከገለጸ በኋላ ተጨማሪ ምክር ሰጠ። (5:1-28) የይሖዋ ቀን የሚመጣው ልክ እንደሌባ ነው። “ሰላምና ዋስትና ያለው ኑሮ ተገኘ” ከሚለው ጩኸት በኋላ ጥፋት በድንገት ይመጣል። ስለዚህ የተሰሎንቄ ክርስቲያኖች በእምነትና በፍቅር ጥሩር፣ የራስ ቁር በሆነው የመዳን ተስፋ እየተጠበቁ በመንፈሣዊ ነቅተው መኖር ነበረባቸው። በጉባዔያቸው ውስጥ ለሚመሩአቸው የጠለቀ አክብሮት ሊኖራቸውና ከክፋት ሁሉ ሊርቁ ይገባቸው ነበር። ለእኛም ቢሆን እንዲሁ ነው።
ጳውሎስ ለተሰሎንቄ ሰዎች የጻፈው የመጀመሪያ መልእክት ለእምነት ባልደረቦቻችን ምስጋናና ማበረታቻ እንድንሰጥ ሊያነሳሳን ይገባል። በተጨማሪም በጠባያችንና በዝንባሌያችን ጥሩ ምሳሌዎች እንድንሆን ሊገፋፋን ይገባል። የተሰጡትም ምክሮች ለይሖዋ ቀን እንድንዘጋጅ ይረዱናል።
[በገጽ 22 ላይ የሚገኝ ሣጥን/ሥዕል]
ጥሩርና የራስ ቁር፦ ጳውሎስ መንፈሳዊ ንቃት እንዲኖረን ሲመክር እንዲህ ሲል ጽፎአል፦ “የእምነትንና የፍቅርን ጥሩር የመዳንንም ተስፋ እንደ ራስ ቁር እየለበስን በመጠን እንኑር።” (1 ተሰሎንቄ 5:8) ጥሩር አንድ ተዋጊ ደረቱን የሚከላከልበት መሣሪያ ሲሆን ከጠፍጣፋ ብረት ከሰንሰለትና ከጠንካራ የእንስሳት ቆዳ ይሠራ ነበር። በተመሳሳይም የእምነት ጥሩር መንፈሳዊነታችንን ይጠብቅልናል። በጥንት ዘመን ይደረግ የነበረው የራስ ቁርስ? የራስ ቁር ከብረታ ብረት ተሰርቶ በአናት ላይ የሚጠለቅ የወታደር ትጥቅ ሲሆን አንድን ወታደር በውጊያ ጊዜ የሚከላከል መሳሪያ ነው። የራስ ቁር የአንድን ጦረኛ ራስ እንደሚጠብቅ ሁሉ የመዳን ተስፋም የአንድን ክርስቲያን የማሰብ ችሎታ በመጠበቅ ፍጹም አቋሙን እንዲጠብቅ ያስችለዋል። የይሖዋ ሕዝቦች ይህን የጦር ትጥቅ መልበሳቸው በጣም አስፈላጊ ነው።—ኤፌሶን 6:11-17