የአምላክ ቃል ኃይለኛ ነው
1. ለ2014 የአገልግሎት ዓመት የተዘጋጀው ልዩ ስብሰባ ጭብጥ ምንድን ነው?
1 ሰዎች ከሠሩት ከየትኛውም ነገር በላቀ ሁኔታ መጽሐፍ ቅዱስ አስተሳሰባችንንና አካሄዳችንን ከይሖዋ ፈቃድ ጋር እንድናስማማ በማድረግ ሕይወታችንን የመለወጥ ኃይል አለው። ይሁንና የአምላክ ቃል ምን ያህል ኃይለኛ አለው? የመለወጥ ኃይሉ በሕይወታችን ውስጥ ሙሉ በሙሉ እንዲሠራ ማድረግ የምንችለው እንዴት ነው? ይበልጥ ውጤታማ በሆነ መንገድ ሌሎችን ለመርዳት ልንጠቀምበት የምንችለውስ እንዴት ነው? እነዚህ ነጥቦች ለ2014 የአገልግሎት ዓመት በተዘጋጀው የልዩ ስብሰባ ቀን ላይ ሲብራሩ ሁላችንም እንደምንበረታታ የታወቀ ነው። የስብሰባው ጭብጥ “የአምላክ ቃል ኃይለኛ ነው” የሚል ሲሆን የተወሰደው ከዕብራውያን 4:12 ነው።
2. ለየትኞቹ ጥያቄዎች የተሰጡትን መልሶች ለማግኘት መጣር ይኖርብናል?
2 ለሚከተሉት ጥያቄዎች የተሰጡትን መልሶች ለማግኘት ሞክሩ፦ በስብሰባው ላይ የሚቀርቡትን ትምህርቶች ስታዳምጡ ለሚከተሉት ጥያቄዎች የሚሰጡትን መልሶች በማስታወሻችሁ ላይ ለመጻፍ ሞክሩ፦
• በይሖዋ ቃል ልንተማመን የሚገባን ለምንድን ነው? (መዝ. 29:4)
• የአምላክ ቃል ያለውን ኃይል በራሳችን ሕይወት ማየት የምንችለው እንዴት ነው? (መዝ. 34:8)
• የአምላክ ቃል ያለውን ኃይል በአገልግሎታችን ልንጠቀምበት የምንችለው እንዴት ነው? (2 ጢሞ. 3:16, 17)
• የሰይጣን ዓለም ባለው የማታለል ኃይል እንዳንሸነፍ ምን ሊረዳን ይችላል? (1 ዮሐ. 5:19)
• ወጣቶች፣ መንፈሳዊ ስኬት ማግኘት የምትችሉት እንዴት ነው? (ኤር. 17:7)
• ስንደክም ብርቱ ወይም ኃይለኛ መሆን የምንችለው እንዴት ነው? (2 ቆሮ. 12:10)
• ሥር የሰደደ ልማድና ዝንባሌ ቢኖረንም እንኳ በቀጣይነት ለውጥ ለማድረግ ምን ሊረዳን ይችላል? (ኤፌ. 4:23)
3. የሚቀርበውን ትምህርት ከማዳመጥ በተጨማሪ ከልዩ ስብሰባው ጥቅም ማግኘት የምንችለው እንዴት ነው?
3 ይህን ጠቃሚ ትምህርት መስማታችን በጣም እንደሚጠቅመን የተረጋገጠ ነው! በተጨማሪም እንደ ወረዳ ስብሰባና አውራጃ ስብሰባ ሁሉ የልዩ ስብሰባው ቀንም ልባችንን ወለል አድርገን ለመክፈትና ከጉባኤያችን ውጪ ከሚገኙ ወንድሞችና እህቶች ጋር አስደሳች ጊዜ ለማሳለፍ አጋጣሚ ይሰጠናል። (መዝ. 133:1-3፤ 2 ቆሮ. 6:11-13) በመሆኑም ይህን አጋጣሚ ከቀድሞ ወዳጆቻችን ጋር ጊዜ ለማሳለፍና አዳዲስ ወዳጆችን ለማፍራት ልንጠቀምበት ይገባል። በስብሰባችሁ ላይ የአውራጃ የበላይ ተመልካች ወይም ቤቴላዊ ወንድም ጎብኚ ተናጋሪ ሆኖ እንዲመጣ የተመደበ ከሆነ ለእሱም ሆነ ለባለቤቱ ሞቅ ያለ አቀባበል ለማድረግ ለምን ጥረት አታደርጉም? በእርግጥም መጪውን የልዩ ስብሰባ ቀን በጉጉት የምንጠባበቅባቸው በርካታ ምክንያቶች አሉን!