የአምላክን ቃል በማንበብ ተደሰት
‘በእግዚአብሔር ሕግ ደስ የሚለው’ ሰው የአምላክን ቃል ‘በቀንና በሌሊት ያስባል።’ (መዝ. 1:1, 2) አንተስ የአምላክን ቃል ማንበብ ያስደስትሃል? የአምላክን ቃል በማንበብ የምታገኘው ደስታ እንዲጨምር ምን ማድረግ ትችላለህ?
ይሖዋ ሲናገር አዳምጥ
ቃላቱን ማንበብህ ብቻውን በቂ አይደለም። የምታነብበውን ነገር በዓይነ ሕሊናህ ሳለው። የተናጋሪዎቹን ድምፅ ለመስማት ሞክር። የመጽሐፍ ቅዱስን የመጀመሪያ ምዕራፎች በምታነብበት ጊዜ ምድርን ለሰው ልጅ ምቹ መኖሪያ ለማድረግ ደረጃ በደረጃ ስለተከናወኑት ነገሮች ይሖዋ ራሱ ሲናገር ስማ። የመጀመሪያዎቹን ሰዎች መፍጠርን በተመለከተ በእርሱ ዘንድ ዋና ሠራተኛ ከነበረው ልጁ ጋር ሲነጋገር አዳምጥ። አዳምና ሔዋን ኃጢአት ሲሠሩ፣ አምላክ በእነርሱ ላይ ፍርድ ሲያስተላልፍ ከዚያም ከገነት ሲያባርራቸው ይታይህ። (ዘፍጥረት ምዕራፍ 1-3) ሕይወቱን ለሰው ልጅ አሳልፎ እንዲሰጥ የተላከውን ኢየሱስ ክርስቶስን በተመለከተ “የምወደው ልጄ ይህ ነው” የሚል ድምፅ ከሰማይ እንደመጣ ስታነብብ በውስጥህ የአክብሮትም የፍርሃትም ስሜት እንዲያድርብህ አድርግ። (ማቴ. 3:16, 17) ይሖዋ “እነሆ፣ ሁሉን አዲስ አደርጋለሁ” ብሎ ሲናገር ሐዋርያው ዮሐንስ ምን ዓይነት ስሜት እንዳደረበት ለመገመት ሞክር። (ራእይ 21:5) በእርግጥም የአምላክን ቃል በዚህ መንገድ ማንበብ የሚያስደስት ነው!
መጽሐፍ ቅዱስን ማንበብህን ከቀጠልህ ይሖዋ ያለው ታላቅ ግርማና ክብር እውን ሆኖ ይታይሃል። ይሖዋ አፍቃሪና ርኅሩኅ ነው። በትሕትና ፈቃዱን ለመፈጸም እስከጣርን ድረስ ያግዘናል እንዲሁም የምናደርገው ሁሉ ይከናወንልን ዘንድ ይደግፈናል። መጽሐፍ ቅዱስ ማንበብህ እንዲህ ያለውን አምላክ ይበልጥ እንድትወድደውና ወደ እርሱ እንድትቀርብ ይገፋፋሃል።—ኢያሱ 1:8፤ መዝ. 8:1 አ.መ.ት ፤ ኢሳ. 41:10
መጽሐፍ ቅዱስ ብዙ ባነበብህ መጠን አምላክ ለአንተ ያለው ዓላማ ይበልጥ እየገባህ ስለሚሄድ የምታገኘው እርካታ የዚያኑ ያህል ይጨምራል። ይሁን እንጂ መጽሐፍ ቅዱስ በማንበብ የምታገኘው ደስታ በዚህ ብቻ የተወሰነ አይደለም። ያነበብከውን ነገር ተጠቅመህ ችግሮችን በጥበብ መፍታት ስትችል ‘ማሳሰቢያዎችህ ድንቆች ናቸው፤ ስለዚህ ነፍሴ ፈለገቻቸው’ እንዳለው መዝሙራዊ ይሰማሃል። (መዝ. 119:129) አንተም ብትሆን አስተሳሰብህንና ምኞቶችህን ከአምላክ ፈቃድ ጋር ለማስማማት የሚረዱ መሠረታዊ ሥርዓቶችን ከመጽሐፍ ቅዱስ ስትማር ደስ ይልሃል።—ኢሳ. 55:8, 9
በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የሚገኙት የሥነ ምግባር መመሪያዎች ከችግር የሚጠብቁን ከመሆናቸውም ሌላ በትክክለኛው ጎዳና እንድንጓዝ ይረዱናል። ይሖዋ ለኃጢአት ምኞቶች መሸነፍ ምን ችግር ሊያስከትልብን እንደሚችል የሚያውቅ አባት መሆኑን የምንገነዘበው መጽሐፍ ቅዱስን ስናነብ ነው። የላቀ ደረጃ ያላቸውን የሥነ ምግባር መመሪያዎቹን መናቅ በሚያስከትለው መጥፎ ውጤት ምክንያት መከራ እንዲደርስብን አይፈልግም። እርሱ ስለ እኛ ያስባል። ሕይወታችንንም በተሻለ መንገድ እንድንመራ ይፈልጋል። ቃሉን ማንበባችን ይሖዋ አምላካችንና ሰማያዊ አባታችን መሆኑ ምን ያህል ትልቅ በረከት እንደሆነ እንድናስተውል ይረዳናል።
መጽሐፍ ቅዱስን በየዕለቱ አንብብ
መዝሙራዊው የአምላክን ቃል በየዕለቱ ስለሚያነብብ ሰው ሲናገር “የሚሠራውም ሁሉ ይከናወንለታል” ብሏል። (መዝ. 1:3) የአምላክን ቃል አዘውትረን ማንበባችንና ሥራ ላይ ማዋላችን ፍጹም ካልሆነው ሥጋችን፣ ከሰይጣን ክፉ ዓለም እንዲሁም ሊውጠን ከሚፈልገው ከዲያብሎስ የሚመጡብንን ተጽዕኖዎች ተቋቁመን ከይሖዋ ጋር ጥሩ ዝምድና እንዲኖረን ያስችለናል።
ይህ ዓለም ብዙ ተጽዕኖ ስለሚያሳድርብን በየዕለቱ ለጥቂት ደቂቃዎችም ቢሆን የአምላክን ቃል ማንበብ ብርታት ሊሰጠን ይችላል። አንዳንዶች በእምነታቸው ምክንያት እስር ቤት ገብተው ሳለ በጋዜጣ ዓምድ ላይ ታትመው ከሚወጡት ጥቂት ጥቅሶች በቀር መጽሐፍ ቅዱስ የማግኘት አጋጣሚ አልነበራቸውም። እነዚህን ጥቅሶች ቀድደው በማውጣትና በቃላቸው በማጥናት ያሰላስሉባቸው ነበር። በአምላክ ቃል ውስጥ የሚገኘውን እውቀት ለመቅሰም አጋጣሚው የፈቀደላቸውን ሁሉ ስላደረጉ ይሖዋ ጥረታቸውን ባርኮላቸዋል። (ዮሐ. 17:3) አብዛኞቻችን ግን መጽሐፍ ቅዱስን እንደልብ የማግኘትና የማንበብ አጋጣሚ አለን። በቀን አንድ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅስ እንደነገሩ ማንበባችን ብቻ ትልቅ ለውጥ ያመጣል ብለን ልንጠብቅ አይገባም። ይሁን እንጂ ፕሮግራሞቻችንን በማስተካከል በየዕለቱ ከመጽሐፍ ቅዱስ የተወሰነ ክፍል ብናነብብ፣ በዚያ ላይ ብናሰላስልና ብንሠራበት እንባረካለን።
ይህ ማለት ግን ሁልጊዜ ይሳካልናል ማለት ላይሆን ይችላል። ፕሮግራማችንን የሚያስተጓጉል ነገር ሲገጥመን መቅደም ያለበትን እናስቀድማለን። ለምሳሌ ያህል ውኃ መጠጣት እንዳለብን እየተሰማን ለአንድ ወይም ለሁለት ቀን ሳንጠጣ አንውልም። በተመሳሳይም ምንም ይምጣ ምን በየዕለቱ የእውነትን ውኃ በመጠጣት ነፍሳችንን የምናረካበት ጊዜ ሊኖረን ይገባል።—ሥራ 17:11
መጽሐፍ ቅዱስን ከዳር እስከ ዳር አንብብ
መጽሐፍ ቅዱስን አንብበህ ጨርሰሃል? አንዳንዶች መጽሐፍ ቅዱስን ከዘፍጥረት እስከ ራእይ ድረስ ማንበብ የማይዘለቅ ነገር ሆኖ ይታያቸዋል። ከዚህ የተነሣ ብዙዎች መጽሐፍ ቅዱስን አንብበው ለመጨረስ በማሰብ ንባባቸውን ከክርስቲያን ግሪክኛ ቅዱሳን ጽሑፎች ጀምረዋል። ለምን? ምናልባት በዚህ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል ውስጥ የሚገኘው መልእክት የክርስቶስን ፈለግ ለመከተል የሚረዳቸው እንዴት እንደሆነ በቀላሉ ማስተዋል ስለሚችሉ ይሆናል። ወይም ደግሞ ከጠቅላላው መጽሐፍ ቅዱስ ከአንድ አራተኛ ብዙም የማይበልጡት የክርስቲያን ግሪክኛ ቅዱሳን ጽሑፎች፣ በመጠን አነስ ብለው ስለሚታዩአቸው ሊሆን ይችላል። ይሁን እንጂ እነዚህን ሃያ ሰባት መጻሕፍት አንብበው ከጨረሱ በኋላ ሠላሳ ዘጠኙን የዕብራይስጥ ቅዱሳን ጽሑፎች ደስ ብሏቸው ማንበብ ቀጥለዋል። አንዴ የዕብራይስጥ ቅዱሳን ጽሑፎቹን አንብበው ከጨረሱ በኋላ መጽሐፍ ቅዱስን የማንበብ ልማድ ስላዳበሩ ለሁለተኛ ጊዜ የግሪክኛ ቅዱሳን ጽሑፎችን ማንበባቸውን ቀጥለዋል። ከዚያ በኋላ የመጽሐፍ ቅዱስ ንባባቸውን አቋርጠው አያውቁም። መጽሐፍ ቅዱስን በየዕለቱ ማንበብ በሕይወት ዘመንህ ሁሉ የምትከተለው ልማድ ይሆን ዘንድ ምኞታችን ነው።
በቤተሰብህ ወይም በጉባኤህ ውስጥ ማንበብ የማይችል ሰው አለ? ካለ ለምን በየዕለቱ መጽሐፍ ቅዱስ አታነብብለትም። አንተም ትጠቀማለህ፤ እርሱም በሰማው ነገር ላይ ሲያሰላስልና በሕይወቱ ውስጥ ሲሠራበት ይጠቀማል።—ራእይ 1:3
ቀስ እያልክ ደግሞ የመጽሐፍ ቅዱስ ንባብህን የሚያዳብር ተጨማሪ ጥረት ማድረግ ትፈልግ ይሆናል። ይህን ማድረግህ የተለያዩ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች እርስ በርስ ያላቸውን ዝምድና ይበልጥ እንድታስተውል ሊረዳህ ይችላል። መጽሐፍ ቅዱስህ ማገናዘቢያ ጥቅሶች ካሉት ስለ አንድ ታሪክ ተጨማሪ ዝርዝር የያዙና ተመሳሳይ ታሪክ የሚገኝባቸው ቦታዎችን ሊጠቁምህ ይችላል። የተለያዩ መዝሙራት እንዲሁም የኢየሱስ ሐዋርያት መልእክቶች ሲጻፉ የነበረውን ሁኔታ እንድታስተውል ሊረዱህ ይችላሉ። ቅዱሳን ጽሑፎችን ጠለቅ ብሎ ማስተዋል (እንግሊዝኛ) የተባለው መጽሐፍ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ስለተጠቀሱ ግለሰቦች፣ ቦታዎችና ባሕርያት ጥልቀት ያለው ተጨማሪ ማብራሪያ ይሰጠናል። በመጽሐፉ ውስጥ ያሉት ሰንጠረዦች ስለ መጽሐፍ ቅዱስ ትንቢት ፍጻሜዎች፣ በተመሳሳይ ዘመን ስለኖሩ ነገሥታትና ነቢያት እንዲሁም ብዙዎቹ የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪኮች ስለተፈጸሙበት ዘመን ይጠቁማሉ።
ባነበብከው ነገር ላይ ስታሰላስል በአምላክ ሕዝብ መካከል የተፈጠሩት አንዳንድ ሁኔታዎች መንስኤያቸው ምን እንደሆነ ግልጽ ይሆንልሃል። እንዲሁም ይሖዋ ከሕዝቡ ጋር በተያያዘ ላደረጋቸው ነገሮች ምክንያቱ ምን እንደሆነ ትረዳለህ። በተጨማሪም ይሖዋ የግለሰቦችን፣ የሕዝቦችንና የመንግሥታትን አድራጎት እንዴት እንደሚመለከት ታስተውላለህ። ይህም የይሖዋን አስተሳሰብ ይበልጥ እንድትረዳ ያስችልሃል።
የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪኮች የተፈጸሙበትን አካባቢ በዓይነ ሕሊናህ መመልከት ከቻልክ ታሪኮቹ ይበልጥ የሚመስጡ ይሆኑልሃል። በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የተጠቀሱትን ቦታዎች የሚያመለክቱ ካርታዎች የቦታዎቹን መልከዓ ምድራዊ አቀማመጥና በመካከላቸው ያለውን ርቀት ሳይቀር ይጠቁማሉ። ለምሳሌ ያህል እስራኤላውያን ቀይ ባሕርን የተሻገሩት በየት በኩል ሊሆን ይችላል? የተስፋይቱ ምድር የቆዳ ስፋት ምን ያህል ነበር? ኢየሱስ ምድራዊ አገልግሎቱን ሲያከናውን ምን ያህል ርቀት ተጉዟል? ጳውሎስ በሚስዮናዊ ጉዞው ወቅት ምን ዓይነት ቦታዎችን ተመልክቷል? ካርታዎችንና መልከዓ ምድራዊ መግለጫዎችን መጠቀም ንባብህን ሕያው የሚያደርጉ ዝርዝር ሁኔታዎችን እንድታስተውል ይረዳሃል። በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የተጠቀሱትን ቦታዎች የሚያሳዩ ካርታዎች የት ልታገኝ ትችላለህ? በአዲሲቱ ዓለም የቅዱሳን ጽሑፎች ትርጉም ላይ የሚገኙ ካርታዎች አሉ። ቅዱሳን ጽሑፎችን ጠለቅ ብሎ ማስተዋል በተባለው መጽሐፍ ጥራዞች ላይም ወደ 70 የሚጠጉ ካርታዎች የሚገኙ ሲሆን በመጀመሪያው ጥራዝ መጨረሻ ላይ የካርታዎች ማውጫ አለ። ሌሎች ካርታዎችን ለማግኘት የመጠበቂያ ግንብ ጽሑፎች ማውጫ መጠቀም ትችላለህ። እነዚህን ጽሑፎች ማግኘት የማትችል ከሆነ በመጽሐፍ ቅዱስ ንባብህ ሊረዱህ የሚችሉትን በመጠበቂያ ግንብ መጽሔቶች ላይ የወጡ ካርታዎችን ተጠቀም።
ንጉሥ ዳዊት በዕብራይስጥ ቅዱሳን ጽሑፎች ውስጥ “አሳቦችህ በእኔ ዘንድ እንደ ምን እጅግ የተከበሩ ናቸው! ቁጥራቸው እንደ ምን በዛ!” በማለት ይሖዋን አወድሷል። (መዝ. 139:17) በክርስቲያን ግሪክኛ ቅዱሳን ጽሑፎች ውስጥ ደግሞ ሐዋርያው ጳውሎስ ‘በክርስቶስ ፊት የክብሩን እውቀት ብርሃን በልባችን ውስጥ በማብራቱ’ ይሖዋን አወድሶታል። (2 ቆሮ. 4:6) ዳዊትና ጳውሎስ የኖሩበት ዘመን የተለያየ ቢሆንም ሁለቱም በአምላክ ቃል ደስ ብሏቸዋል። አንተም ይሖዋ በመንፈሱ ባስጻፈው ቃሉ ውስጥ ያሰፈረልህን መልእክት በሙሉ፣ ጊዜ መድበህ በማንበብ ደስታ ማግኘት ትችላለህ።