የጥያቄ ሣጥን
◼ በምንሞትበት ጊዜ ሀብታችንን በሙሉ ወይም የተወሰነውን ለይሖዋ ድርጅት ማውረስ ብንፈልግ አስቀድመን ልናስብበት የሚገባው ነገር ምንድን ነው?
አንድ ሰው ከሞተ በኋላ በቁሳዊ ንብረቱ ላይ ሊያዝ አይችልም። (መክ. 9:5, 6) በመሆኑም አንዳንድ ወንድሞች ለጊዜው አያስፈልገንም የሚሉትን ገንዘብ ለይሖዋ ድርጅት በአደራ መልክ ይሰጣሉ፤ ይህ “ተመላሽ ሊሆን የሚችል ገንዘብ የሚሰጥበት ዝግጅት” ተብሎ ይጠራል። ሌሎች ደግሞ ያላቸውን የማይንቀሳቀስ ንብረት በሕይወት እስካሉ ድረስ የሚጠቀሙበት ቢሆንም በሚሞቱበት ጊዜ የይሖዋ ድርጅት እንዲወርሰው አስቀድመው ዝግጅት ያደርጋሉ። ብዙውን ጊዜ እንዲህ ያሉትን ዝግጅቶች ያለምንም ችግር ተግባራዊ ማድረግ የሚቻል ቢሆንም አንዳንድ ጊዜ እንቅፋቶች ያጋጥማሉ። ስለሆነም ብዙዎች ንብረታቸውን ለማን ማውረስ እንደሚፈልጉ የሚገልጽ ኑዛዜ ወይም ሕጋዊ ሰነድ አስቀድመው ያዘጋጃሉ። (2 ነገ. 20:1) አብዛኛውን ጊዜ ይህ ሕጋዊ ሰነድ ባለንብረቱ ጉዳዩን እንዲያስፈጽምለት የወከለውን ወይም ባለአደራ የሚሆነውን ሰው ማንነት ይጠቅሳል። እንዲህ ዓይነት ሰነድ ካልተዘጋጀ ግን በብዙ አገሮች የሟቹ ንብረት የሚከፋፈለው በባለሥልጣናት ውሳኔ ወይም በአካባቢው በሚሠራበት ልማድ መሠረት ይሆናል። ስለዚህ ሀብታችንን በሙሉ ወይም የተወሰነውን ለይሖዋ ድርጅት ማውረስ የምንፈልግ ከሆነ ይህን ፍላጎታችንን የሚገልጽ ሕጋዊ ሰነድ ማዘጋጀት ብሎም ጉዳይ አስፈጻሚ ወይም ባለአደራ የሚሆንልንን ሰው በጥንቃቄ መምረጣችን በጣም አስፈላጊ ነው።
ጉዳይ አስፈጻሚው ወይም ባለአደራው ከባድ ኃላፊነት እንዳለበት ሊታወቅ ይገባል። በተለይ ሟቹ ብዙ ሀብት ካለው ንብረቱን ማሰባሰብና በተገቢው መንገድ ማከፋፈል ብዙ ሥራና ጊዜ ሊጠይቅ ይችላል። በተጨማሪም የመንግሥት ባለሥልጣናት ያወጧቸው ተግባራዊ ሊደረጉ የሚገቡ መመሪያዎች ሊኖሩ ይችላሉ። አንድ ሰው የጉባኤው አባል ስለሆነ ብቻ ጥሩ ጉዳይ አስፈጻሚ ወይም ባለአደራ ይሆናል ማለት አይቻልም። ለዚህ ዓላማ የምንመርጠው ሰው ብቃት ያለው፣ እምነት የሚጣልበትና ፍላጎታችንን ለማስፈጸም ፈቃደኛ የሆነ መሆን ይኖርበታል።—በታኅሣሥ 8, 1998 ንቁ! (እንግሊዝኛ) ገጽ 24 ላይ የወጣውን “ዘ ዊዝደም ኤንድ ቤኔፊትስ ኦቭ ኧስቴት ፕላኒንግ” የሚለውን ርዕስ እንዲሁም የጥር 15, 1998 መጠበቂያ ግንብ ገጽ 19ን ተመልከት።