የሃይማኖታዊ አክራሪነት መስፋፋት
ሃይማኖታዊ አክራሪነት [ፋንዳሜንታሊዝም] ከጥቂት አሥርተ ዓመታት በፊት በፕሮቴስታንት እምነት ውስጥ ብቻ የሚታይ የጥቂቶች እንቅስቃሴ ነበር። ዛሬ ግን ሁኔታዎች በእጅጉ ተለውጠዋል! የሃይማኖት ተንታኝ የሆኑት ብሩስ ሎውሬንስ ከዛሬ 30 ዓመት በፊት ሃይማኖታዊ አክራሪነትa በ20ኛው መቶ ዘመን መጨረሻ ላይ መገናኛ ብዙሐንን በሰፊው የሚያወያይና በዩኒቨርሲቲ ደረጃ ጥናት የሚደረግበት ዐቢይ ርዕስ ይሆናል ብለው ያሰቡ በጣም ጥቂቶች እንደነበሩ ጽፈዋል።
ይሁንና ዛሬ እውነታው ይህ ነው። ጋዜጦች በዓምዶቻቸው የሚዘግቧቸው የኃይል እርምጃ የታከለባቸው ትዕይንተ ሕዝቦች፣ የነፍስ ግድያዎች፣ ፀረ ውርጃ እንቅስቃሴዎች፣ ሃይማኖታዊ የንቅናቄ ቡድኖች የሚያካሂዱት ፖለቲካዊ እንቅስቃሴ እንዲሁም አምላክን የሚያዋርዱ ናቸው የሚባሉትን መጻሕፍት በአደባባይ ማጋየት የሃይማኖታዊ አክራሪዎችን እንቅስቃሴ ዘወትር ያስታውሱናል። በኢጣሊያ የሚታተመው ሳምንታዊው የፋይናንስ ጋዜጣ ሞንዶ ኤኮኖሚኮ ሃይማኖታዊ አክራሪነት በየትኛውም ቦታ “በአምላክ ስም ጥፋት እየፈጸመ” ነው ሲል አትቷል።
ሃይማኖታዊ አክራሪዎች ብዙውን ጊዜ ሴራ ጠንሳሾች እንዲሁም የአሸባሪነት ጥቃቶችን የሚፈጽሙ ጽንፈኞችና ወግ አጥባቂዎች እንደሆኑ ተደርገው ይታያሉ። ሰዎች እንደ ሮማ ካቶሊኩ ኮሙኒዮን አ ሌብራዚኦና፣ የአይሁድ እምነቱ ጋሽ ኤሙኔም እንዲሁም የሰሜን አሜሪካው የፕሮቴስታንት ክርስቺያን ኮዋሊሽን ያሉት ቡድኖች እየተበራከቱ መምጣታቸው ያስፈራቸዋል። ሃይማኖታዊ አክራሪነት በመስፋፋት ላይ ያለው ለምንድን ነው? የዚህ እንቅስቃሴ መንሥኤው ምንድን ነው? ምናልባት ፈረንሳዊው የሶሺዮሎጂ ተመራማሪ ዢል ከፔል እንደጠቆሙት “የአምላክ የበቀል እርምጃ” ይሆን?
[የግርጌ ማስታወሻ]
a ሃይማኖታዊ አክራሪ [ፋንዳሜንታሊስት] የሚባለው ባሕላዊና ጥንታዊ የሆኑ ሃይማኖታዊ ሥርዓቶችን በግትርነት የሚከተል ሰው ነው። “ፋንዳሜንታሊዝም” የሚለው ቃል ትርጉም በሚቀጥለው ርዕስ ውስጥ በሰፊው ይብራራል።
[በገጽ 3 ላይ የሚገኝ የሥዕል ምንጭ]
Nina Berman/Sipa Press