የታማኝነት ምሳሌ ትተዋል
1 የሙሉ ጊዜ አገልግሎት ዘርፍ የሆነው ልዩ አቅኚነት የተጀመረው በ1937 ነበር። በክርስቲያናዊ አገልግሎት ተሞክሮ ያካበቱና ጥሩ ችሎታ ያላቸው ወንዶችና ሴቶች ድርጅቱ በመደባቸው በየትኛውም ቦታ ሄደው ለማገልገል ራሳቸውን በፈቃደኝነት አቀረቡ። ይህ ከሆነ አሥርተ ዓመታት የተቆጠሩ ቢሆንም ልዩ አቅኚዎች አሁንም ሊኮረጅ የሚገባው የታማኝነት ምሳሌ እየተዉ ይገኛሉ።—ዕብ. 6:12
2 ግንባር ቀደም ሆነው አገልግለዋል:- ልዩ አቅኚዎች በተንቀሳቃሽ የሸክላ ማጫወቻ በመጠቀም ከቤት ወደ ቤት እየሄዱ በመስበክ ረገድ ግንባር ቀደሞቹ ናቸው። እንዲሁም በተመላልሶ መጠየቅ ወቅት መጽሐፍ ቅዱሳዊ ውይይት ለማድረግ የተቀዱ ሸክላዎችን ይጠቀሙ ነበር። እንዲህ ያደርጉ የነበረው ጉባኤዎች በተቋቋሙባቸው በትላልቅ ከተሞች ነበር። ከጊዜ በኋላ ግን የመንግሥቱ ሰባኪዎች ይበልጥ ወደሚያስፈልጉባቸው ቦታዎች ተላኩ። በሄዱበት ቦታም ፍላጎት ያላቸውን ሰዎች ተከታትለው በመርዳት የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት ያስጀምሩ ነበር። እነርሱ ባደረጉት ከፍተኛ ጥረት በመቶዎች የሚቆጠሩ አዳዲስ ጉባኤዎች ሊቋቋሙ ችለዋል። የምሥራቹን ደከመኝ ሰለቸኝ ሳይሉ መስበካቸው ዛሬ በድርጅቱ ውስጥ ለሚታየው መስፋፋት ከፍተኛ አስተዋጽኦ አበርክቷል። (ኢሳ. 60:22) ልዩ አቅኚዎች ምሥራቹን “ከሰማይ በታች ላለ ፍጥረት ሁሉ” በማድረሱ ሥራ አሁንም ከፍተኛ ሚና እየተጫወቱ ይገኛሉ።—ቈላ. 1:23
3 ልንኮርጃቸው ይገባል:- አንዳንድ ልዩ አቅኚዎች ለአሥርተ ዓመታት በሙሉ ጊዜ አገልግሎት አሳልፈዋል። ዓመታት እያለፉ ሲሄዱም እነዚህ ታማኝ ወንዶችና ሴቶች በተለያዩ ሁኔታዎች እምነታቸው ተፈትኗል። (1 ጴጥ. 1:6, 7) ይበልጥ እርዳታ ወደሚያስፈልጋቸው ቦታዎች ሄደው ለማገልገል ሲሉ ሊያገኙ የሚችሉትን ቁሳዊ ጥቅም እርግፍ አድርገው ትተዋል። በአሁኑ ወቅት አንዳንዶቹ በዕድሜ የገፉ ከመሆናቸውም ሌላ የተሟላ ጤንነት የላቸውም ወይም እየታገሉት ያለ ሌላ ችግር አለባቸው። (2 ቆሮ. 4:16, 17) ይህም ሆኖ “ባረጁ ጊዜ እንኳ ያፈራሉ።” (መዝ. 92:14) ትምክህታቸውን በይሖዋ ላይ ስለጣሉ የእርሱ በረከት አልተለያቸውም።—መዝ. 34:8፤ ምሳሌ 10:22
4 ልዩ አቅኚዎች በእርግጥም ከፍተኛ ምስጋና ሊቸራቸው ይገባል። ልዩ አቅኚዎች በጉባኤያችሁ ተመድበው የሚያገለግሉ ከሆነ አብራችኋቸው ብዙ ጊዜ በማሳለፍ ከተሞክሯቸው መጠቀም ትችላላችሁ። ታማኝ የመንግሥቱ አዋጅ ነጋሪዎች ሆነው ላከናወኑት አገልግሎት አድናቆት እንዳላችሁ አሳዩ። እንዲሁም የእነርሱ ጽናት የብርታት ምንጭ ይሁንላችሁ። የእነርሱን እምነት የሚኮርጁ ሁሉ የይሖዋን ሞገስና በረከት ያገኛሉ። ምክንያቱም ይሖዋ ‘ቃላቸውን በሚጠብቁ ታማኝ ሰዎች ይደሰታል።’—ምሳሌ 12:22 የ1980 ትርጉም