ያለማሰለስ ስበኩ
1 አንዳንድ ጊዜ፣ የአገልግሎት ክልላችን በተደጋጋሚና በጥራት ቢሸፈንም በጎ ምላሽ የሚሰጡ ሰዎች ቁጥር አነስተኛ እንደሆነ ይሰማን ይሆናል። ይሁንና ምሥራቹን መስበካችንን እንድንቀጥል የሚገፋፉ አሳማኝ ምክንያቶች አሉ።—ማቴ. 28:19, 20
2 ምሥክር እንዲሆን:- ኢየሱስ እንደተናገረው የመንግሥቱን ምሥራች የመስበኩ ሥራ፣ “የዓለም መጨረሻ” መቅረቡን የሚጠቁመውና የተለያዩ ክንውኖችን ያቀፈው ምልክት ጉልህ ገጽታ ነው። ይህ ሥራ የሚከናወነው “ለሕዝብ ሁሉ ምስክር እንዲሆን” ነው። (ማቴ. 24:3, 14) የመንግሥቱን ምሥራች በመስበኩ ሥራ መካፈላችን በራሱ ለሚመለከቱን ሰዎች ሁሉ ታላቅ ምሥክርነት ይሰጣል። አንዳንድ ሰዎች መልእክቱን ለመስማት ፈቃደኛ ባይሆኑም እንኳ አካባቢውን ለቅቀን ከሄድን በኋላ ለሰዓታት ምናልባትም ለቀናት ስለ እኛ ያወሩ ይሆናል። የምናገለግልበትን ምክንያት መረዳታችን በስብከቱ ሥራ እንድንጸና ይረዳናል። ምሥክርነት በመስጠትና የማስጠንቀቂያ መልእክት በማሰማት የመጽሐፍ ቅዱስ ትንቢት ፍጻሜ እንዲያገኝ የበኩላችንን ድርሻ ስናበረክት ይሖዋን እናስደስተዋለን።—2 ተሰ. 1:6-9
3 መጽናት ያስፈልጋል:- የሰዎችን ሐሳብ የሚከፋፍሉና ጊዜያቸውን የሚሻሙ በርካታ ነገሮች በመኖራቸው ፍላጎታቸውን ለማሳደግ መጣር ጽናት ይጠይቅብናል። አንዲት ሴት፣ ከይሖዋ ምሥክሮች ጋር መጽሐፍ ቅዱሳዊ ውይይት ለማድረግ ፈቃደኛ የሆነችው በየሳምንቱ ለአንድ ዓመት ያህል ተመላልሶ መጠየቅ ከተደረገላት በኋላ ነበር። በሰማችው ነገር በጣም ስለተደሰተች መጽሐፍ ቅዱስን እንድታጠና የቀረበላትን ግብዣ ተቀበለች። ይህቺ ሴት በስብሰባዎች ላይ መገኘት የጀመረች ሲሆን በቅርቡ የመጠመቅ ፍላጎት እንዳላትም ገልጻለች።
4 በዓለም ላይ ያሉት ሁኔታዎች በፍጥነት እየተለዋወጡ ሲሆን የሰዎች አመለካከትም በዛው መጠን ይቀያየራል። ከዚህ በፊት መልእክቱን ሊቀበሉን ፈቃደኞች ያልነበሩ ብዙ ሰዎች በአሁኑ ጊዜ፣ የምንነግራቸውን አስደሳች ተስፋ ለመስማት ፈቃደኞች ሊሆኑ ይችላሉ። ለመንግሥቱ መልእክት በጎ ምላሽ የሰጠው አንድ ሰው ብቻ እንኳ ቢሆን መጽናታችን የሚያስቆጨን አይሆንም።
5 በምድር ላይ ‘እየተሠራ ባለው ጸያፍ ተግባር የሚያዝኑና የሚያለቅሱ’ ሰዎች ቁጥር ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ ሄዷል። (ሕዝ. 9:4) የመንግሥቱ አዋጅ ነጋሪዎች ቁጥር ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ መምጣቱ የጽድቅ ዝንባሌ ያላቸው እነዚህ ሰዎች ለመንግሥቱ መልእክት ምላሽ በመስጠት ላይ መሆናቸውን ያሳያል። (ኢሳ. 2:2, 3) ስለዚህ ጽኑ ሆነን ለሰዎች ‘መልካም ዜና በማብሰር’ ያለማሰለስ መስበካችንን እንቀጥል።—ኢሳ. 52:7፤ ሥራ 5:42