ራእይ—ታላቁ መደምደሚያው ደርሷል!
1 “ዘመኑ ቀርቦአል፤ እንግዲህ ይህን የትንቢት ቃል የሚያነብ ብፁዕ ነው፤ የሚሰሙትና የተጻፈውንም የሚጠብቁ ብፁዓን ናቸው።” (ራእይ 1:3) በራእይ መጽሐፍ ውስጥ የተጠቀሱት አብዛኞቹ ትንቢቶች ፍጻሜያቸውን እያገኙ ባሉበት ዘመን ውስጥ የምንኖር እንደመሆናችን መጠን እነዚህ ቃላት የዮሐንስ ራእይ ያለውን ጠቀሜታ ያጎላሉ። በመሆኑም ራእይ—ታላቁ መደምደሚያው ደርሷል! የተባለውን መጽሐፍ ከጥር 8, 2007 ጀምሮ በጉባኤ መጽሐፍ ጥናት ላይ ማጥናታችን የተገባ ነው።
2 ራእይ—ታላቁ መደምደሚያው ደርሷል! የተባለውን መጽሐፍ ለመጨረሻ ጊዜ በጉባኤ መጽሐፍ ጥናት ላይ ካጠናን ወዲህ የዚህ ዓለም መልክ በብዙ መንገድ ተለውጧል። (1 ቆሮ. 7:31) ከዚህም በተጨማሪ የአምላክን መንግሥት ምሥራች በመስበኩ ሥራ በቅርቡ መሳተፍ የጀመሩ ብዙ አስፋፊዎች፣ ይህን መጽሐፍ ቁጥር በቁጥር የማጥናት አጋጣሚ አላገኙም። ራእይ—ታላቁ መደምደሚያው ደርሷል! የተባለውን መጽሐፍ ማጥናታችን ሁላችንም ከፊት ለፊታችን የሚጠብቀንን ነገር በንቃት እንድንጠብቅ ያስችለናል።—ራእይ 16:15
3 በእያንዳንዱ ሳምንት በሚደረገው ጥናት ላይ ለመገኘት ግብ አውጡ። ይህ ትምህርት ነቅተን እንድንጠብቅ የሚረዳን ከመሆኑም ሌላ ኢየሱስ ለሰባቱ ጉባኤዎች የላካቸው መልእክቶች መንፈሳዊነታችንን እንዲሁም በአገልግሎት የምናደርገውን እንቅስቃሴ በእጅጉ ሊጎዱ ከሚችሉ ሁኔታዎች እንድንርቅ የሚረዳን ሐሳብ እናገኝባቸዋለን።—ራእይ 1:11, 19
4 በደንብ ተዘጋጁ:- በእያንዳንዱ መጽሐፍ ጥናት ላይ ከመገኘታችሁ በፊት በራእይ መጽሐፍ ላይ የሚገኙትንና በዚያ ሳምንት የሚብራሩትን ጥቅሶች በሙሉ አንብቧቸው። እንዲሁም ለጥቅሶቹ የተሰጡትን ቅዱስ ጽሑፋዊ ማብራሪያዎች ለማስተዋል ሞክሩ። ልባችሁ በትምህርቱ እንዲነካ ዋና ዋና ነጥቦችን በሚገባ ለመረዳት ጥረት አድርጉ። (ነህ. 8:8, 12) ለማሰላሰል እንዲሁም ራሳችሁን እንደሚከተሉት ያሉ ጥያቄዎችን ለመጠየቅ ጊዜ መድቡ:- ‘ይህ ነጥብ ስለ ይሖዋና ዓላማውን ከግብ ለማድረስ ስለሚያደርገው ነገር ምን ያስተምረኛል? አኗኗሬን ከዓላማው ጋር ማስማማት ብሎም ሌሎችም እንዲሁ እንዲያደርጉ መርዳት የምችለው እንዴት ነው?’
5 ‘የጌታ ቀን’ በ1914 ከጀመረ ዘጠና ሁለት ዓመታት አልፈዋል። (ራእይ 1:10) ከፊት ለፊታችን በራእይ መጽሐፍ ውስጥ በትንቢት የተገለጹት ትልቅ ቦታ የሚሰጣቸው ክስተቶች ይጠብቁናል። ራእይ—ታላቁ መደምደሚያው ደርሷል! የተባለውን መጽሐፍ ማጥናታችን ለልባችንና ለአእምሯችን እረፍት የሚያስገኝ ከመሆኑም በተጨማሪ ‘ሁሉን የሚችለው አምላክ ታላቅ የጦርነት ቀን’ እና አዲሱ ዓለም እንደቀረበ ያለንን እምነት ያጠናክርልናል።—ራእይ 16:14፤ 21:4, 5