በምታገኙት አጋጣሚ ሁሉ ተጠቀሙበት
1. እውነቱን ማወቅ የተባለውን ትራክት ምን ለማድረግ ልንጠቀምበት እንችላለን?
1 እውነቱን ማወቅ ትፈልጋለህ? የሚለው ትራክት የተዘጋጀው የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት ለማስጀመር እንድንጠቀምበት ታስቦ ነው። ይሁን እንጂ ይህ ትራክት የእውነትን ዘር ለመዝራት የሚያገለግል ጠቃሚ መሣሪያም ነው። (መክ. 11:6) ይህን ትራክት በጥሩ ሁኔታ መጠቀም እንድንችል የሚረዱ አንዳንድ ሐሳቦች ከዚህ በታች ቀርበዋል።
2. እውነቱን ማወቅ የሚባለውን ትራክት ውይይት ለመጀመር ልንጠቀምበት የምንችለው እንዴት ነው?
2 ውይይት ለመጀመር፦ ትራክቱን ለቤቱ ባለቤት ሰጥተን በትራክቱ የፊት ገጽ ላይ ያሉትን ስድስት ጥያቄዎች ካሳየነው በኋላ “ከእነዚህ ጥያቄዎች መካከል የየትኛውን መልስ ማወቅ ይፈልጋሉ?” በማለት መጠየቅ እንችላለን። የቤቱን ባለቤት መልስ ካዳመጥክ በኋላ ግለሰቡ ለመረጠው ጥያቄ መጽሐፍ ቅዱስ ምን መልስ እንደሚሰጥ ለማወቅ በትራክቱ ላይ ውይይት አድርጉ፤ እንዲሁም ከጥቅሶቹ መካከል አንዱን አንብብለት። በትራክቱ የመጨረሻ ገጽ ላይ ያለውን ሐሳብ አንብበህለት ወይም በአጭሩ ነግረኸው የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት የሚባለውን መጽሐፍ አበርክትለት። የቤቱ ባለቤት መጽሐፉን መውሰድ ባይፈልግ እንኳ ትራክቱን ትተንለት መሄዳችን የእውነት ዘር በልቡ ውስጥ ሥር እንዲሰድ ሊያደርግ ይችላል።—ማቴ. 13:23
3. የቤቱ ባለቤት ሥራ ላይ ከሆነ ምን ልናደርግ እንችላለን?
3 የቤቱ ባለቤት ሥራ ላይ ከሆነ፦ እንዲህ ማለት እንችላለን፦ “ሥራ ላይ ስለሆኑ ይህን ትራክት ትቼልዎት ልሂድ። ትራክቱ ብዙዎቻችንን የሚያሳስቡ ስድስት ጥያቄዎች የሚያነሳ ከመሆኑም በላይ መጽሐፍ ቅዱስ ለእያንዳንዱ ጥያቄ የሚሰጠውን መልስ ይዟል። ሌላ ጊዜ ስመጣ ደግሞ የእርስዎን ሐሳብ ያካፍሉኛል።”
4. በመንገድ ላይ ስናገለግል ትራክቱን ለማበርከት ምን ማለት እንችላለን?
4 በመንገድ ላይ ስናገለግል፦ እንዲህ ማለት እንችላለን፦ “ጤና ይስጥልኝ፤ እዚህ ላይ ያሉትን ጥያቄዎች ጠይቀው ያውቃሉ? [ሐሳቡን እንዲገልጽ ዕድል ስጠው።] ይህ ትራክት በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ የሚገኘውን ግልጽና አጥጋቢ የሆነ መልስ ይዟል።” ግለሰቡ የማይቸኩል ከሆነ ደግሞ በትራክቱ ላይ ካሉት ጥያቄዎች መካከል በአንዱ ላይ መወያየት እንዲያውም የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት የሚባለውን መጽሐፍ ማበርከት እንችል ይሆናል።
5. ሰዎችን ቤታቸው ካላገኘናቸው አንዳንድ ጊዜ ትራክቱን እንዴት ልንጠቀምበት እንችላለን?
5 በቤታቸው ላልተገኙ ሰዎች፦ በአንዳንድ ክልሎች ውስጥ አስፋፊዎች ቤት ላልተገኙ ግለሰቦች፣ በመንገድ የሚያልፉ ሰዎች ሊያዩ በማይችሉበት ቦታ ላይ ጽሑፎችን አስቀምጠው ይሄዳሉ። በክልላችሁ ውስጥ እንዲህ ማድረግ የተለመደ ከሆነ አንዳንድ ጊዜ፣ እውነቱን ማወቅ የተባለውን ትራክት አስቀምጣችሁ መሄድ ትችሉ ይሆን? በሌላ ጊዜ ተመልሳችሁ ስትሄዱ እንዲህ ማለት ትችላላችሁ፦ “ከዚህ በፊት በመጣንበት ወቅት እርስዎ ቤት ውስጥ ስላልነበሩ ይህንን ትራክት አስቀምጠንልዎት ሄደን ነበር። ከእነዚህ ጥያቄዎች መካከል የየትኛውን መልስ ማወቅ ይፈልጋሉ?”
6. እውነቱን ማወቅ የተባለው ትራክት የስብከቱን ሥራ ለማከናወን ጠቃሚ መሣሪያ እንዲሆን ያደረገው ምንድን ነው?
6 እውነቱን ማወቅ የተባለው ትራክት እውነትን ቀለል ባለና ባልተወሳሰበ መልኩ ያቀርባል። በመሆኑም ማንኛውም ዓይነት ሃይማኖትና ባሕል ያላቸውን ሰዎች ትኩረት ይስባል። ይህን ትራክት ልጆችም ሆኑ አዲስ አስፋፊዎች በቀላሉ ሊያበረክቱት ይችላሉ። አንተስ በምታገኘው አመቺ አጋጣሚ ሁሉ በዚህ ትራክት እየተጠቀምክ ነው?