እሁድ፣ ሐምሌ 27
ማበረታታትም ሆነ . . . መውቀስ [የሚችል] ሊሆን ይገባል።—ቲቶ 1:9
ጎልማሳ ክርስቲያን መሆን ከፈለጋችሁ ጠቃሚ ክህሎቶችን ማዳበር ይኖርባችኋል። እንዲህ ማድረጋችሁ በጉባኤ ውስጥ ኃላፊነት ለመቀበል፣ ራሳችሁን ወይም ቤተሰባችሁን ለማስተዳደር የሚያስችል ሥራ ለመያዝ እንዲሁም ከሌሎች ጋር ጥሩ ዝምድና ለመመሥረት ይረዳችኋል። ለምሳሌ ጥሩ የማንበብና የመጻፍ ችሎታ አዳብሩ። መጽሐፍ ቅዱስ ደስተኛና ስኬታማ የሆነ ሰው በየዕለቱ የአምላክን ቃል እንደሚያነብና እንደሚያሰላስልበት ይናገራል። (መዝ. 1:1-3) አንድ ሰው መጽሐፍ ቅዱስን በየዕለቱ ማንበቡ የይሖዋን አስተሳሰብ ለመረዳት ያስችለዋል፤ ይህ ደግሞ አጥርቶ ለማሰብና በሚገባ ለማመዛዘን ይረዳዋል። (ምሳሌ 1:3, 4) ወንድሞቻችንና እህቶቻችን በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ የተመሠረተ መመሪያና ምክር ለማግኘት ብቃት ያላቸው ወንድሞች እርዳታ ያስፈልጋቸዋል። ጥሩ የማንበብና የመጻፍ ችሎታ ካላችሁ ግንዛቤ የሚያሰፉና እምነት የሚያጠናክሩ ንግግሮችንና ሐሳቦችን መዘጋጀት ትችላላችሁ። በተጨማሪም ጥሩ ማስታወሻ በመያዝ እምነታችሁን ማጠናከር እንዲሁም ሌሎችን ማበረታታት ትችላላችሁ። w23.12 26-27 አን. 9-11
ሰኞ፣ ሐምሌ 28
ከእናንተ ጎን ያለው፣ ከዓለም ጎን ካለው ይበልጣል።—1 ዮሐ. 4:4
ፍርሃት በሚሰማህ ጊዜ ይሖዋ ወደፊት ሰይጣን ሲጠፋ በሚያደርገው ነገር ላይ አሰላስል። በ2014 የክልል ስብሰባ ላይ የቀረበ አንድ ሠርቶ ማሳያ አንድ አባት 2 ጢሞቴዎስ 3:1-5 በገነት ውስጥ የሚኖረውን ሕይወት የሚገልጽ ቢሆን ኖሮ ምን ይል እንደነበር ከልጆቹ ጋር ሲወያይ አሳይቶን ነበር፦ “በአዲሱ ዓለም እጅግ አስደሳች የሆነ ዘመን እንደሚመጣ ይህን እወቅ። ምክንያቱም ሰዎች ሌሎችን የሚወዱ፣ መንፈሳዊ ሀብት የሚወዱ፣ ልካቸውን የሚያውቁ፣ ትሑቶች፣ አምላክን የሚያወድሱ፣ ለወላጆች የሚታዘዙ፣ የሚያመሰግኑ፣ ታማኝ የሆኑ፣ ለቤተሰባቸው ጥልቅ ፍቅር ያላቸው፣ ለመስማማት ፈቃደኞች የሆኑ፣ ሁልጊዜ ስለ ሌሎች መልካም ነገር የሚያወሩ፣ ራሳቸውን የሚገዙ፣ ገሮች፣ ጥሩ ነገር የሚወዱ፣ ታማኞች፣ እሺ ባዮች፣ ራሳቸውን ዝቅ የሚያደርጉ፣ ሥጋዊ ደስታን ከመውደድ ይልቅ አምላክን የሚወዱ ይሆናሉ፤ ከልብ ለአምላክ ያደሩ ናቸው፤ ከእነዚህ ጋር የጠበቀ ወዳጅነት ይኑርህ።” በአዲሱ ዓለም ስለሚኖረው ሕይወት ከቤተሰቦችህ ወይም ከእምነት ባልንጀሮችህ ጋር የመወያየት ልማድ አለህ? w24.01 6 አን. 13-14
ማክሰኞ፣ ሐምሌ 29
በአንተ ደስ ይለኛል።—ሉቃስ 3:22
መጽሐፍ ቅዱስ “ይሖዋ በሕዝቡ ደስ ይሰኛል” ይላል። (መዝ. 149:4) በእርግጥም ይሖዋ በቡድን ደረጃ በሕዝቡ እንደሚደሰት ማወቅ በጣም የሚያጽናና ነው! ይሁንና አንዳንዶች ተስፋ ሲቆርጡ ‘ይሖዋ በግለሰብ ደረጃ በእኔ ይደሰት ይሆን?’ የሚል ጥርጣሬ ይፈጠርባቸዋል። በጥንት ዘመን የኖሩ የይሖዋ ታማኝ አገልጋዮች ከእንዲህ ዓይነት ስሜት ጋር የታገሉበት ወቅት ነበር። (1 ሳሙ. 1:6-10፤ ኢዮብ 29:2, 4፤ መዝ. 51:11) መጽሐፍ ቅዱስ በግልጽ እንደሚያሳየው ፍጹማን ያልሆኑ ሰዎች የይሖዋን ሞገስ ማግኘት ይችላሉ። ታዲያ በእሱ ዘንድ ተቀባይነት ማግኘት የምንችለው እንዴት ነው? በኢየሱስ ክርስቶስ ማመን እንዲሁም መጠመቅ ይኖርብናል። (ዮሐ. 3:16) ይህን ስናደርግ ከኃጢአታችን ንስሐ እንደገባንና የአምላክን ፈቃድ ለማድረግ ለእሱ ቃል እንደገባን በሕዝብ ፊት እናሳያለን። (ሥራ 2:38፤ 3:19) ይሖዋ የእሱ ወዳጆች ለመሆን ስንል እነዚህን እርምጃዎች መውሰዳችን ያስደስተዋል። ራሳችንን ስንወስን ከገባነው ቃል ጋር ተስማምተን ለመኖር የምንችለውን ሁሉ እስካደረግን ድረስ ይሖዋ ይደሰትብናል፤ እንደ ቅርብ ወዳጆቹ አድርጎም ይመለከተናል።—መዝ. 25:14፤ w24.03 26 አን. 1-2